Search

የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በክረምት ተረኛ ችሎት የሚያስተናግዳቸውን አስቸኳይ ጉዳዮች ይፋ አደረገ

ማክሰኞ ሐምሌ 28, 2018 50

በፌደራል ፍርድ ቤቶች አዋጅ ቁጥር 1234/2013 አንቀጽ 38 ንዑስ አንቀጽ 3 መሠረት፤ ከመደበኛ የፍርድ ቤት የሥራ ጊዜ ውጭ አስቸኳይ ጉዳዮች የሚስተናገዱበት አሰራር ተዘርግቶ ሲሠራ ቆይቷል።

በዚሁ መሠረት መሠረታዊ የመብት ጥሰት የሚያስከትሉ በባሕሪያቸው ጊዜ የማይሰጡ እና አፋጣኝ ውሳኔ ካልተሰጠባቸው ሊካስ የማይችል ጉዳት የሚያስከትሉ አጣዳፊ ጉዳዮችን አይቶ መወሰን አስፈላጊ በመሆኑ፤ ፍርድ ቤቶች በከፊል ዝግ በሚሆኑበት ከነሐሴ 01 እስከ መስከረም 30 ቀን ባለው ጊዜ ውስጥ በተረኛ ችሎት አገልግሎት ይሰጣል።

በፍትሐ ብሔር በኩል በሚታዩ ጉዳዮች፡ አስቸኳይ የእግድ አቤቱታዎች፣ የልጅ ቀለብ፣ አካል ነጻ የማውጣት አቤቱታዎች፣ እንቅስቃሴን ገዳቢ በሆኑ ጉዳዮች ላይ የሚቀርቡ አቤቱታዎች፣ ሠራተኞች በአሠሪዎቻቸው ላይ የሚያቀርቧቸው የደመወዝ ክፍያ አፈጻጸሞች፣ ከግልግል ዳኝነት ትዕዛዝ ጋር ተያይዘው የሚቀርቡ አስቸኳይ የማኅተም አገልግሎት ጥያቄዎች እንዲሁም ሌሎች ጊዜ የማይሰጡ ጉዳዮች በተረኛ ችሎት ይስተናገዳሉ።

በወንጀል በኩል ደግሞ፡ የዋስትና፣ የአመክሮ፣ የአርቲዲ (እስረኛ ያላቸው የወንጀል መዛግብት) በሰበር የሚቀርቡ አቤቱታዎች፣ የአራዳ ምድብ ችሎት ጊዜ ቀጠሮ፣ ለመሰየም የሚቀርብ አቤቱታ እና ሌሎች መደበኛ የሥራ ጊዜን መጠበቅ የማይችሉ አጣዳፊ የወንጀል ጉዳዮች የሚታዩ ይሆናል።

በመሆኑም ፍርድ ቤቶች በከፊል ዝግ በሚሆኑበት በዚህ ወቅት ተገልጋዮች እና የፍርድ ቤቱ ማኅበረሰብ አሠራሩን ተገንዝበው አስፈላጊውን ትብብር እንዲያደርጉ የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ጥሪ አቅርቧል።

 

አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: