የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን በአሶሳ ዞን፣ ቡልድግሉ ወረዳ የአቅመ ደካማ ቤቶች ግንባታ በማስጀመር የተለያዩ ድጋፎችንም አድርገዋል።
ርዕሰ መስተዳድሩ በዚሁ ወቅት፣ የመደመር መንግሥት የዜጎችን ኑሮ ለማሻሻል የጀመረው እና በሕዝባዊ ንቅናቄ እየተከናወነ የሚገኘው የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት የበርካቶችን ሕይወት እየቀየረ መሆኑን ተናግረዋል።
የመተሳሰብ እና የመረዳዳት ባሕል የሆነው የበጎ ፈቃድ አገልግሎትን በማጠናከር ሁለንተናዊ ብልፅግናን ለማረጋገጥ መጠቀም እንደሚገባ ገልጸዋል።
በተያዘው ዓመት በክልሉ ከ200 በላይ የአቅመ ደካማ ቤቶች በአዲስ መልክ የሚገነቡ ሲሆን፣ ከ50 በለይ ቤቶች ደግሞ ይታደሳሉ ብለዋል።
የተለያዩ ተቋማት በተለያዩ አካባቢዎች የቤት ግንባታ እና የተለያዩ ሰብዓዊ ድጋፎች እያከናወኑ መሆኑን ጠቅሰው፣ ይህን ተግባር አጠናክሮ በማስቀጠል የኢትዮጵያን የመረዳዳት ባሕል ወደ ላቀ ደረጃ ማሸጋገር እንደሚገባ ገልጸዋል።
ርዕሰ መስተዳደሩ በአሶሳ ዞን፣ ቡልድግሉ ወረዳ ለ200 ተማሪዎች የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍ እና ለ200 አቅመ ደካሞች የማዕድ ማጋራት ያከናወኑ ሲሆን፣ ለ5 አቅመ ደካሞች ደግሞ የመኖሪያ ቤት ግንባታ አስጀምረዋል።
ድጋፍ የተደረገላቸው ዜጎች ምስጋና በማቅረብ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል።
በነስረዲን ሀሚድ
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: