ኢትዮጵያ የምስራቅና ደቡባዊ አፍሪካ ሀገራት በወንጀል ድርጊት የተገኘ ገንዘብ ወይም ንብረትን ሕጋዊ አስመስሎ የማቅረብ ወንጀል መከላከል ቡድን ጉባዔን የሚሳተፉ እንግዶችን እየተቀበለች ይገኛል።
ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ ከ2013 ጀምሮ በፋይናንስ ደህንነት አገልግሎት በኩል አባል በመሆን በመሳተፍ ላይ ስትሆን የተቋሙ የወቅቱ ፕሬዚዳንት በመሆን በማገልገል ላይ ትገኛለች፡፡
ጉባዔው ከነገ ጀምሮ እስከ ነሐሴ 24 ቀን 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን የሚካሄድ ሲሆን ከ1150 በላይ ልዑካን ቡድኖች ይሳተፉበታል፡፡
የፋይናንስ ደህንነት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር አቶ ሙሉቀን አማረ ዛሬ በሰጡት መግለጫ፤ ስብሰባውን በስኬት ለማጠናቀቅ አስፈላጊው ዝግጅት መጠናቀቁን አስታውቀዋል።
ጉባዔው በሕገ ወጥ የሰዎች ዝውውር፣ በሙስና ፣ በሕገ ወጥ የገንዘብ እና የዕፆ ዝውውር የተገኘን ገንዘብን በተመለከተ፣ ሽብርተኝነትን በገንዘብ መርዳት፣ ጅምላ ጨራሽ መሳሪያዎችን ስርጭት ጨምሮ ሌሎች ወንጀሎችን በቅንጅት ለመከላከል አጋርነትን ለማጠናከር ያለመ ነው፡፡
በስብሰባው ላይ ከፖሊሲ አውጪዎች፣ ከፋይናንስ ደህንነት ተቋማት፣ ከሕግ አስከባሪ አካላት፣ ከግሉ የፋይናንስ ዘርፍ ተቋማት እንዲሁም ከዓለም አቀፍ ተቋማት የልዑካን ቡድኖችና ተወካዮች የተውጣቱ ከ1150 በላይ ተወካዮች እንደሚሳተፉ ይጠበቃል፡፡
ሕገ ወጥ የገንዘብ ዝውውር ሽብርተኝነትን በገንዘብ መርዳት ድንበር ተሸጋሪ ወንጀሎች በመሆናቸው ዓለም አቀፋዊ ይዘት ስላላቸው ሁሉም በትብብር መስራት ካልቻለ መካላከል እንደማይቻል አቶ ሙሉቀን ተናግረዋል፡፡
በወንጀል የተገኘ ገንዘብ ወይም ድርጊትን ሕጋዊ አስመስሎ ማቅረብ፤ ሽብርተኝነትና ጅምላ መሳሪያዎችን ብዛትን የመከላከል እና መቆጣጠርን ዓላማ ያደረገው ጉባዔ በስኬት እንዲጠናቀቅ ሁሉም ዜጋ ኃላፊነቱን እንዲወጣ ጠይቀዋል፡፡
እ.ኤ.አ በ1999 በታንዛኒያ የተመሰረተው ቀጣናዊ ተቋም ከ21 አባል ሀገራት በተውጣጡ የፋይናንስ ደኅንነት ተቋማት፣ የዓለም ባንክ፣ ዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅትን ጨምሮ 34 አጋር ተቋማትን እና ሀገራትን የያዘ ነው፡፡
በላሉ ኢታላ