የሶር ፏፏቴ በኦሮሚያ ክልል ኢሉአባቦር ዞን በቾ ወረዳ ውስጥ ነው የሚገኘው፡፡
ፏፏቴው ከኢሉ አባቦር ዞን መቱ ከተማ በቅርብ ርቀት ላይ የሚገኝ የቱርስት መስህብ ቢሆንም መሰረተ ልማቶች ባለመሟላታቸው በጎብኝዎች ዘንድ ብዙም ሳይታወቅ ቆይቷል፡፡
ሶር የተሰኘው ወንዝ የፏፏቴው መነሻ ሲሆን፤ ወንዙ የመቱን ከተማ አቋርጦ የሚያልፍ ነው፡፡
በስፋቱም ሆነ በርዝመቱ ከጢስ ዓባይ ቀጥሎ ትልቅ እንደሆነ የሚነገርለት ሶር ፏፏቴ፤ ወቅቶች ሲፈራረቁ የፏፏቴው መጠን ከፍ እና ዝቅ እንደሚል ይነገራል፡፡
ይህ የተፈጥሮ መስህብ ትኩረት ተሰጥቶት መልማት ቢችል በቱሪዝም ዘርፉ ለሀገር ኢኮኖሚ የድርሻውን ገቢ ማበርከት የሚችል የተፈጥሮ ሀብት መሆኑ ይገለፃል፡፡
ዙሪያውን በተፈጥሮ ቡና እና ጥቅጥቅ ባለ ደን የተከበበው ሶር ፏፏቴ፣ የቱሪስቶችን ቀልብ ለመግዛት የሚያስችል አስደናቂ መልክዓ ምድርንም የተላበሰ ነው፡፡
50 ሜትር ቁመት እና 78 ሜትር የጎን ስፋት ያለው ፏፏቴው፤ ወደ ታች በሚንደረደርበት ወቅት ልክ እንደ ጢስ ዓባይ ለአካባቢው ልዩ ውበት እንደሚያላብሰው ይነገራል፡፡
የሶር ፏፏቴ ከአስደናቂ መልክዓ ምድሩ በተጨማሪ፤ እንደ ዝንጀሮ፣ ጉሬዛ እና ድኩላ ያሉ የዱር እንስሳትን አስጠልሎ ይገኛል፡፡
በመሐመድ ፊጣሞ
#ebc #ebcdotstream #Ethiopia #Metu #ሶርፏፏቴ