የጣናነሽ ጀልባ ለባህዳር እና አካባቢው ማህበረሰብ ትልቅ ትርጉም ያላት፤ ለጎብኚዎችም የቆይታቸው ትዝታ የተከተበባት ናት።
የዕድሜያቸውን ግማሽ ሲዘውሯት፣ እክል ሲያጋጥማት ሲያስጠግኗት፣ ከአካባቢው ነዋሪ እስከ እንግዳ ይዘውባት ሲጓዙ ለነበሩት ካፒቴን ስጦታው ግን ከጀልባም በላይ መሆኗን ይገልፃሉ።
ትውልድ እና ዕድገታቸው በማዕከላዊ ጎንደር ጣቁሳ ወረዳ የሆነው አቶ ስጦታው አባታቸው ካፒቴን በነበሩ ወቅት አብረዋቸው በጀልባ ይመላለሱ እንደነበር ያስታውሳሉ።
ታዲያ ራስን የመቻል ጉዞ ሲጀመር በቀድሞ የጣና ሐይቅ ትራንስፖርት በቀን ሥራ ላይ መሰማራታቸውን ለኢቢሲ ዶትስሪም ተናግረዋል።
ከዕድገታቸው በተጨማሪ ይህ ዕድል ውሏቸው በጣና ሐይቅ እና በዙሪያው ባሉ ጀልባዎች አቅራቢያ እንዲሆን አስቻለ።
በቀን ሥራ ከዚያም በቲኬት ቆራጭነት የጀመረው የሥራ ሕይወታቸው በ1988 ዓ.ም የጀርመን ስሪት የሆነችው እና 27 ሜትር ርዝማኔ ያላት የጣናነሽ ጀልባ ረዳት ካፒቴን ለመሆን አበቃቸው።
እናም ላለፋት 30 ዓመታት የጣናነሽን በመዘወር ውሏቸውን በጣና ሐይቅ ላይ አደረጉ።
በዚህ ቆይታቸው በጣና ሐይቅ እና በዙሪያው ያሉ ደሴቶች የጎብኚዎችን አፍ በአድናቆት ሲያስከፍቱ ስለመመልከታቸው ይናገራሉ።
በጉዞ ወቅት በተለይም ማዕበል ሲነሳ ሰዎች የሚያሳዩት የፍርሃት ሁናቴ እና ድርጊታቸውም ሌላው ተደጋጋሚ ገጠመኛቸው እንደሆነ በትውስታ ያወሳሉ።
አሁን ጀልባዎች እየተበራከቱ መምጣታቸውን በመጥቀስ በጀልባ ዘዋሪነት ብሎም ጥገና ላይ የምንፈልገውን ያህል ባለሙያ አለን ወይ? የሚለው አሳሳቢ ስለመሆኑ ይናገራሉ።
የእርሳቸው ሙያ በልምድ የተገኘ መሆኑን በማንሳትም ዛሬ ላይ ግን ከዚያ በተሻለ ዘርፉን የሚመጥኑ ባለሙያዎች ልናፈራ ይገባል ይላሉ።
በቅርቡ ወደ ጣና ሐይቅ ለመግባት በዝግጅት ላይ ያለችው የጣናነሽ2 ጀልባም ለጉብኝትና ለዓመታዊ ክብረ በዓላት ወደ ደሴቶቹ ለሚያቀኑ ተሳፋሪዎች ምቹ መጓጓዣ እንደምትሆን እምነቴ ሲሉም ገልፀዋል ካፒቴን ስጦታው።
በአፎሚያ ክበበው
#ኢቢሲዶትስትሪም #ባህርዳር #የጣናነሽ