በዓላትንና የመንግስት ሠራተኞች ደሞዝ ጭማሪን አስመልክቶ የዋጋ ንረት እንዳይኖር ትኩረት ተደርጎ እየተሰራ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር አባይ ተናገሩ።
ሕገ-ወጥ የንግድ እንቅስቃሴ የሚያደርጉ አካላት ላይ ሕብረተሰቡ ጥቆማ መስጠት ይገባዋልም ብለዋል ምክትል ከንቲባው።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የገበያ ማረጋጋት ሕገ-ወጥ ንግድ ቁጥጥርና የኢትዮጵያ-አዲስ አበባ ታምርት ንቅናቄ ግብረ ኃይል፤ የዘመን መለወጫ የበዓል ገበያን አስመልክቶ እና ከዋጋ ጭማሪ ጋር ተያይዞ ለመገናኛ ብዙኃን መግለጫ ሰጥቷል።
የኑሮ ውድነትን ለመቀነስ፣ ገበያን ለማረጋጋት እና አቅርቦትን ለማስፋት የሚያስችሉ 219 የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች መኖራቸውን፤ እንዲሁም አምስት የገበያ ማዕከላት በከተማ ደረጃ ሰፊ አገልግሎት እየሰጡ መሆናቸውን በመግለጫው ተጠቅሷል።
በኤዶም አማረ