የኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ያዘጋጀው የ10 ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድ አፈፃፀም በተለይ ባለፉት አምስት ዓመታት አበረታች ውጤቶች የታዩበት መሆኑ ተመላከተ።
ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ያዘጋጀው የ10 ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድ አፈፃፀም ግምገማ የፍርድ ቤቱ ፕሬዚዳንት አቶ ጋዛሊ አባሲመልን ጨምሮ ከወረዳ እስከ ዞን ያሉ ፍርድ ቤቶች ፕሬዚዳንቶች በተገኙበት በነቀምቴ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል።
የኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ለውጥ ለማምጣት እና የፍርድ ቤቶችን አፈፃፀም ለማሳደግ ከ2013 - 2022 ድረስ የሚቆይ የ10 ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድ አውጥቶ ወደ ሥራ መግባቱ ይታወቃል።
በነቀምቴ ከተማ በተካሄደው የግምገማ መድረክ በስትራቴጂክ ዕቅዱ አጋማሽ ላይ የታዩ ጎድለቶች እና ጠንካራ ጎኖች በስፋት ተገምግመዋል።
በተለይ ባለፉት አምስት ዓመታት ስትራቴጂክ ዕቅዱን ወደ ተግባር ከመለወጥ አንፃር በተለያዩ እርከኖች የተሠሩ ሥራዎች አበረታች መሆናቸው ተነሥቷል።
በፍርድ ቤቶች በተከናወነ የሪፎርም ሥራ በ2015 ዓ.ም 71.5 በመቶ የነበረውን የተገልጋዮች የዕርካታ መጠን በ2017 ዓ.ም ወደ 85.5 በመቶ ማሳደግ መቻሉ ተጠቁሟል።
ከኢ-ፋይል ጋር በተያያዘም ከዚህ በፊት የነበረው አፈፃፀም ደካማ ቢሆንም አሁን ግን የአቤቱታ ቁጥር እና የኢ-ፋይል አተገባበር እኩል እየሆነ መምጣቱ ተገልጿል።
የሐሰት መረጃ፣ የዳኞች ነፃነት ጉዳይ፣ ከኑሮ ውድነት ጋር በተያያዘ ዳኞች ሥራ እየለቀቁ መሆኑ እና እነርሱን ለመተካት አስቸጋሪ ሁኔታ መፈጠሩ ትኩረት ሊሰጣቸው የሚቡ ጎድለቶች መሆናቸው በመድረኩ ተነሥቷል።
በኦላና ያዴሳ
#EBC #ebcdotstream #EtvAfaanOromoo #justice