ለኢሬቻ ሆረ ፊንፊኔ ክብረ በዓል አስፈላጊው ቅድመ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ ሥራ አስኪያጅ ጽ/ቤት አስታወቀ።
በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ ዋና ሥራ አስኪያጅ ኢንጅነር ወንድሙ ሴታ ከኢቢሲ ዶትስትሪም ጋር በነበራቸው ቆይታ፥ በያዝነው ሳምንት የሚከበረው ኢሬቻ ሆረ ፊንፊኔ ባማረ መልኩ በሰላም እንዲከበር የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል።
በመስከረም ወር በመዲናችን በርካታ እንግዶች እና ነዋሪዎች የሚታደሙባቸው ሁለት ታላላቅ ሃይማኖታዊ እና ህዝባዊ የአደባባይ በዓላት ባማረ መልኩ እንዲከበሩ ጽ/ቤቱ ከማዕከል እስከ ወረዳ በዘረጋው መዋቅሩ ላለፈው አንድ ወር በቅንጅት ሲሠራ መቆየቱን ተናግረዋል።
በደመራና መስቀል በዓልም አስቀድሞ በተከናወነ ተገቢ ግንዛቤ የመፍጠር ሥራ በሁሉም አካባቢዎች በተከናወነው የደመራ ማብራት ሥርዓት ምንም ዓይነት አደጋ ሳያጋጥም ባማረና በደመቀ መልኩ መከበሩን ኢንጅነር ወንድሙ አስታውሰዋል።
የአደባባይ በዓል የሆነው ኢሬቻ ሆረ ፊንፊኔ በርካታ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ሀገራት ጎብኚዎች የሚታደሙበት በመሆኑ፤ ባማረ እና ከአደጋ ስጋት ነፃ በሆነ መልኩ እንዲከበር የከተማ ፅዳት እና ውበት፣ የቅድመ አደጋ መከላከል እና የኤሌክትሪክ አገልግሎት አሰጣጥ ሥራዎችን በተናበበ መልኩ ለማከናወን ጽ/ቤቱ የሚያደርገውን ድጋፍና ክትትል አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ኢንጅነር ወንድሙ ሴታ ገልጸዋል።
በሜሮን ንብረት
#EBCdotstream #Irreecha #HoraFinfine