በዓለም ላይ ካሉ ታላላቅ ሙዚየሞች አንዱ የሆነው እና በፈረንሳይ ፓሪስ የሚገኘው ሉቭር ሙዚየም ባልታወቁ ግለሰቦች ተዘርፎ በናፖሊዮን ዘመነ መንግሥት የነበሩ ቅርሶች መወሰዳቸው ታውቋል።
ትናንት በተፈጸመውና ከአራት እስከ ሰባት ደቂቃ ብቻ እንደፈጀ በተገመተው በዚህ ዘረፋ፣ ቁጥራቸው ለጊዜው ያልታወቀ ዘራፊዎች የጭነት መኪና ላይ የተገጠመ መሰላል በመጠቀም ወደ ሙዚየሙ ቅጥር ግቢ ከገቡ በኋላ ዘጠኝ የሚደርሱ በፈረንሳዩ ናፖሊዮን ዘመነ መንግሥት የነበሩ ዋጋቸው የማይተመን ቅርሶችን መውሰዳቸው ተነግሯል።
ለረጅም ጊዜ በተጠና ሁኔታ የተከናወነ እንደሆነ በተገመተው በዚህ ዘረፋ፣ ዘራፊዎቹ ከእይታ ተሰውረው የሙዚየሙን መስኮት በመስበር ወንጀሉን ፈጽመዋል።
በመላው ፓሪስ ዘራፊዎቹን የመፈለግ ሥራ ተጠናክሮ የቀጠለ ሲሆን፣ ፖሊስ እነዚህን በዋጋ የማይተመኑ ቅርሶች ለማግኘት ኅብረተሰቡ እንዲተባበር ጥሪ አቅርቧል።
ከ380 ሺህ በላይ ከሚሆኑት አጠቃላይ ቅርሶች ውስጥ፣ ሊዮናርዶ ዳ ቪንቺ የሳላትን ታዋቂዋን የሞናሊዛን ስዕል ጨምሮ ከ35 ሺህ በላይ የተለያዩ ቅርሶችን ብቻ ለእይታ የሚያቀርበው ሉቭር ሙዚየም፣ በዓለም ላይ ከፍተኛ ጥበቃ ከሚደረግላቸው ሙዚየሞች አንዱ እንደሆነ ይታወቃል።
በዋሲሁን ተስፋዬ
#EBC #ebcdotstream #artifacts