ኢትዮጵያ የኅልውናዋ ጉዳይ የሆነውን ቀይ ባህርን እንድታጣ ያደረገውን ውሳኔ ማን ወሰነ? የሚለውን ወሳኝ ጥያቄ ማቅረብ ተገቢ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቀይ ባህርን በተመለከተ በሰጡት ማብራሪያ፣ “የቀይ ባህር ጉዳይ ሕጋዊ፣ ታሪካዊ፣ መልከዓ ምድራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ጥያቄ ነው ብለን እናምናለን፤ ይህንን በተረጋጋ መንገድ ማየት ያስፈልጋል” ብለዋል።
‘የኢትዮጵያን የቀይ ባህር የማጣት ውሳኔ ማን ወሰነ?’ ብለን ስንፈልግ ተቋማት አልገቡበትም፤ ይህን የሚያህል የኅልውና ጉዳይ ማን እንደወሰነ መጠየቅ ተገቢ ነው ሲሉም አክለዋል።
ኢትዮጵያ ተዘግቶባት መኖር እንደማትችል ገልጸው፣ “ለጎረቤቶቻችን መናገር የምንፈልገው ኢትዮጵያ ስታድግ ለቀጣናውም ልማት ምንጭ ትሆናለች” ብለዋል።
የኢትዮጵያ ፍላጎትም በትብብር ማደግ መሆኑን ነው በማብራሪያቸው ያስታወቁት።