የኢንዱትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሰሃ ይታገሱ (ዶ/ር) የአውሮፓ እና የፈረንሳይ ኩባንያዎች በድሬዳዋ ነጻ የንግድ ቀጣና እንዲሰማሩ ጥሪ አቀረቡ።
ዋና ሥራ አስፈጻሚው በፈረንሳይ፣ ፓሪስ እየተካሄደ በሚገኘው የኢትዮጵያ እና የአውሮፓ የኢንቨስትመንት ፎረም ላይ ከተገኙ የአውሮፓ እና የፈረንሳይ የኩባንያ ባለቤቶች ጋር ተወያይተዋል።
ዶ/ር ፍሰሃ በዚሁ ወቅት፥ ባለሀብቶቹ በድሬዳዋ ነጻ የንግድ ቀጣና ሀብታቸውን እና ዕውቀታቸውን ሥራ ላይ ለማዋል ከወሰኑ፤ ኮርፖሬሽኑ ደረጃውን የጠበቀ መሠረተ ልማት እና የአንድ ማዕከል አገልግሎት እንደሚያቀርብላቸው ገልጸዋል።

የሀገሪቱን ስትራቴጂያዊ ኢንቨስትመንቶች ዕድገት ለመደገፍ የሚያስፈልገው የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ መሠረተ ልማት ዘርፍ ለውጪ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ክፍት መደረጉን ጠቅሰው፤ ሀገሪቱ በዘርፉ ያሏትን የኢንቨስትመንት አማራጮች አብራርተዋል።
ኮርፖሬሽኑ የውጪ ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ሀብታቸውን ሥራ ላይ ሲያውሉ ቆይታቸው ውጤታማ እንዲሆን የተቻለውን ሁሉ እንደሚያደርግ ዋና ሥራ አስፈጻሚው ቃል ገብተዋል።
የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን በሚያስተዳድራቸው 14 ልዩ የኢኮኖሚ ዞኖች እና ፓርኮች ውስጥ ከ200 በላይ የሚሆኑ ኩባንያዎች በሥራ ላይ የሚገኙ ሲሆን፤ ኩባንያዎቹ ከ100 ሺህ ለሚበልጡ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር ችለዋል።
#ebcdotstream #ethiopia #europe #france #investment