የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የጊዜ ሠሌዳ ይፋ አድርጓል።
በዚሁ መሠረት የምርጫ ድምፅ የሚሰጥበት ቀን ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም እንደሆነ የጊዜ ሠሌዳው አመላክቷል።
ቦርዱ እስካሁን ስለሠራቸው የቅድመ-ምርጫ ሥራዎች በተመለከተ እና በተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ ለመገናኛ ብዙኃን ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ሜላትወርቅ ኃይሉ በ2018 ዓ.ም ለሚያከናውነው 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የተለያዩ የቅድመ-ምርጫ ተግባራትን በማከናወን ላይ መሆኑን አስታውቀዋል።
በቦርዱ የፀደቀ የ7ኛው ሀገራዊ ምርጫ የጊዜ ሠሌዳ ይፋ የተደረገ ሲሆን በዚህም መሠረት የዕጩዎች ምዝገባ ከጥር 1 እስከ የካቲት 1/2018 ዓ.ም ይካሄዳል።
የምረጡኝ ቅስቀሳ /የምርጫ ዘመቻ/ ከጥር 1 እስከ ግንቦት 19/2018 ዓ.ም የሚካሄድ ሲሆን፣ የመራጮች ምዝገባ ከየካቲት 7 እስከ መጋቢት 7/2018 ዓ.ም እንደሚከናወን በጊዜ ሠሌዳው ተመላክቷል።
ሆኖም የመራጮች ምዝገባን ራስን በራስ መመዝገብ ከጥር 15 ጀምሮ እስከ መጋቢት 7 ማድረግ እንሚቻል ተገልጿል።
የ7ኛው ሀገራዊ ምርጫ የድምፅ መስጫ ቀን ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም እንደሚሆን ይፋ የተደረገ ሲሆን፣ ይፋዊ የምርጫ ውጤት መግለጫ ቀን ሰኔ 4/2018 ዓ.ም መሆኑን ቦርዱ ይፋ አድርጓል።
በሞላ ዓለማየሁ