ከማህበራዊ ሚዲያ ፕላትፎርም አንዱ የሆነውን ቲክቶክ በመጠቀም ከሀገራችን ባህልና ወግ ያፈነገጡ መልዕክቶችና ምስሎችን ሲያስተላልፉ የነበሩ ግለሠቦችን በቁጥጥር ስር በማዋል ምርመራ እየተጣራባቸው ይገኛል።
በቲክቶክ ስሙ Lil_jay ወይም ጎይጋር ኮት ውይዋል እና ከእርሱ ጋር ያልተገባ አፀያፊ ድርጊት ስትፈጽም የነበረችው ኸሊሌ ጊቦ አያና የተባሉ ግለሠቦች የቲክቶክ አካውንትን በመጠቀም ለመልካም ጠባይና ስነ ምግባር ተቃራኒ የሆነ መልዕክትንና ተንቀሳቃሽ ምስልን በቀጥታ ሲያስተላልፉ በመገኘታቸው ታህሳስ 02 ቀን 2018 ዓ.ም በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ፣ ወረዳ 9 ልዩ ስሙ ፍሊንትስቶን ሆምስ ከሚባል ቦታ በቁጥጥር ስር ውለዋል።

በተመሳሳይ በቲክቶክ ስሙ ፕሬዚዳንት ማሜ ወይም ባህሩዲን ሙሰማ ከሀገራችን ባህልና ወግ ያፈነገጡ መልዕክቶችን ሲያስተላልፍ በቦሌ ክፍለ ከተማ፣ ወረዳ 1 ልዩ ቦታው ቦሌ ሚካኤል ጃፋር መስጅድ አካባቢ በቁጥጥር ስር ውሏል።

ማህበራዊ ሚዲያን ለበጎ ተግባራትና ትውልድን ለማነጽ መጠቀም ሲገባ ትውልድን ወደ አላስፈላጊ ድርጊት እንዲገባ የሚያስተምሩና የሚገፋፉ መሠል እኩይ ተግባራትን በሚፈጽሙ ግለሠቦችና ቡድኖች ላይ የሚወሰደው ሕጋዊ ርምጃ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የአዲስ አበባ ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ አስታውቋል።