ታላቁ የኢትዮጵያ ኅዳሴ ግድብ ቀጣናዊ ትስስርን ለመፍጠር ያለው ሚና ከፍተኛ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትሩ የምሥራቅ አፍሪካ ጉዳዮች አማካሪ ሚኒስትር አቶ ጌታቸው ረዳ ገለጹ።
ግድቡ ወንድማማችነትን ከማጎልበት ያለፈ ሚና እንዳለውም በጉባ በተካሄደው “ስለ ኢትዮጵያ” የውይይት መድረክ ላይ አንስተዋል።
ኢትዮጵያ የኅዳሴ ግድቡን ግንባታ ስትጀምርም ሆነ ስታጠናቅቅ የተለያዩ ፈተናዎችን አስተናግዳለች ያሉት ሚኒስትሩ፤ ከግድቡ መጠናቀቅ በኋላ የሚገጥሙ የፈተና ዓይነቶችና መጠናቸው ሊቀየር እንደሚችል ጠቁመዋል። ይህም ግድቡ ለኢትዮጵያ ተጨማሪ ጉልበትና የዲፕሎማሲ አቅም የሚፈጥር በመሆኑ ነው ብለዋል።
ኢትዮጵያ ደጋግማ ስለ ኃይል አቅርቦት የምታነሳው ይህንን በመገንዘብና ዘርፉ ብሔራዊ አቅም የሚገነባበት ዋነኛ መሣሪያ በመሆኑ ነው ያሉት አቶ ጌታቸው፤ የምናልመውን የዕድገት ደረጃ እውን ለማድረግ በኢነርጂ ዘርፉ ላይ ሙሉ ትኩረትንና ጊዜን ማዋል ይገባል ሲሉ ገልጸዋል።
በአሸናፊ አንዳለ