Search

ኢትዮጵያ እና ቱርክዬ በጋራ ለመፈፀም የተግባቡባቸው የስምምነት አጀንዳዎች እና ነጥቦች

ማክሰኞ የካቲት 10, 2018 43

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከፕሬዚዳንት ረጀብ ጠይፕ ኤርዶዋን ጋር በብሔራዊ ቤተመንግሥት በሰጡት የጋራ መግለጫ ሁለቱ ሀገራት በጋራ ለመፈፀም የተግባቡባቸውን የስምምነት አጀንዳዎች እና ነጥቦች ዘርዝረዋል።

 

I. የንግድ እና ኢኮኖሚ ትብብር 

የንግድ ልውውጥ መጠን፦ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የንግድ ልውውጥ ቢያንስ ወደ አንድ ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ እና ከዚያም በላይ ለማሳደግ ታቅዷል።

የዘርፍ ብዝሃነት (Diversification)፦ የንግድ ግንኙነቱ በተወሰኑ ምርቶች ላይ ብቻ ሳይወሰን የተለያዩ የቢዝነስ ዘርፎችን እንዲያካትት ስምምነት ላይ ተደርሷል።

የቱርክዬ ኢንቨስትመንት፦ ታዋቂ የቱርክዬ ኩባንያዎች በኢትዮጵያ ኢንቨስት በማድረግ ለሀገር ውስጥ እና ለጠቅላላው የአፍሪካ ገበያ የሚሆኑ ምርቶችን እንዲያመርቱ እና ኤክስፖርት እንዲያደርጉ ድጋፍ ለማድረግ ተስማምተዋል።

 

II. የባህር በር እና ዲፕሎማሲያዊ ድጋፍ 

 ኢትዮጵያ ያቀደችውን የ10.2 በመቶ ዕቅድ ለማሳካት የባህር በር ወሳኝ መሆኑ ተገልጿል።

ለኢትዮጵያ ዕድገት ማነቆ (bottleneck) የሆነውን የሎጂስቲክስ ችግር ለመፍታት የባህር በር ቁልፍ መሆኑ ታምኖበታል።

ኢትዮጵያ በሰላማዊ መንገድ የባሕር በር እንድታገኝ ቱርክዬ በዲፕሎማሲው መስኩ የራሷን ጫና በመፍጠር የበኩሏን ሚና እንድትጫወት ከስምምነት ተደርሷል።

 

III. የፀረ-ሽብር ትግል እና አካባቢያዊ ጉዳዮች 

ኢትዮጵያ እና ቱርክዬ በፀረ-ሽብር ትግሉ ዙሪያ በጋራ ለመሥራት ተስማምተዋል።

የአየር ንብረት ለውጥን በተመለከተ ቱርክዬ ዘንድሮ የምታዘጋጀውን የኮፕ (COP) ስብሰባ በሚቀጥለው ዓመት ለኢትዮጵያ የምታስረክብ በመሆኑ፣ በዝግጅት ሂደት ውስጥ የልምድ ልውውጥ እና መደጋገፍ ለማድረግ ተስማምተዋል።

 

IV. ሥልታዊ እና ቀጣናዊ ግንኙነት 

አፍሪካ በቀጣይ 20 እና 30 ዓመታት ውስጥ የሚኖራትን ከፍተኛ የኢኮኖሚ ሚና ከግምት ውስጥ በማስገባት፣ ቱርክዬ በአፍሪካ ዕድገት ውስጥ ያላትን የጂኦግራፊያዊ እና ኢኮኖሚያዊ ሚና እንድትወጣ መግባባት ላይ ተደርሷል።

በኢትዮጵያ እና በቱርክዬ መካከል ያለውን ጥንታዊ ግንኙነት በመከባበር እና በመደጋገፍ ላይ ተመሥርቶ ይበልጥ ለማጠናከር መሪዎቹ ቃል ገብተዋል።

 

#Ethiopia #Turkiye #Diplomacy #AbiyAhmedAli #RecepTayyipErdoğan #EthiopianBroadcastingCorporation #EBC #EBCdotstream