የአፍሪካ ኩራትና የደንበኞቹ የልብ አድራሽ የሆነው የኢትዮጵያ አየር መንገድ፤ ባለፉት ሰማንያ ዓመታት በጽናት ተጉዞ ለዛሬው ዓለም አቀፍ ዝናው በቅቷል።
አየር መንገዱ ሁሌም የከፍታ መገለጫ ቢሆንም፤ በተለይ ባለፉት ስምንት የለውጥ ዓመታት ያስመዘገበው ውጤት ግን ታሪክን የደገመና እጅግ አስገራሚ ሆኖ ተመዝግቧል።
በሰኔ 2010 ዓ.ም ሀገራዊ ለውጥ ሲመጣ የነበረው የ100 አውሮፕላኖች ቁጥር፤ በታህሳስ 2017 ዓ.ም ከ170 በላይ በመድረስ ታላቅ ዕድገት አሳይቷል።
ባለፉት ስምንት ዓመታት ብቻ ከ74 በላይ አዳዲስና ዘመናዊ አውሮፕላኖችን ወደ ሥራ ያስገባው አየር መንገዱ፤ ይህ የቁጥር ዕድገት በገቢው ላይም ከፍተኛ ለውጥ እንዲመዘገብ አድርጓል።
በዚህም በ2010 ዓ.ም የነበረው የ2.4 ቢሊየን ዶላር ዓመታዊ ገቢ፤ በ2017 ዓ.ም ወደ 7.6 ቢሊዮን ዶላር በማደግ የ216.67 በመቶ ብልጫ ማሳየቱ ተረጋግጧል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ የንግድ ዘርፍ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ለማ ያደቻ እንደሚሉት፤ ይህ ስኬት የተገኘው ተቋሙ በአንድ የገቢ ምንጭ ላይ ብቻ ባለመወሰን የተቀናጀ የንግድ ሞዴልን ተግባራዊ በማድረጉ ነው።
አየር መንገዱ አካዳሚውን ወደ አቪዬሽን ዩኒቨርሲቲ በማሳደግ የመቀበል አቅሙን 4 ሺህ ያደረሰ ሲሆን፤ ባለፉት ስምንት ዓመታት ካሰለጠናቸው 10 ሺህ በላይ ባለሙያዎች መካከል 99 በመቶዎቹ በድርጅቱ ውስጥ ተቀጥረው በማገልገል ላይ ይገኛሉ።
ከጥገና አገልግሎት ባለፈ በካርጎ፣ በኬተሪንግ፣ በሆስፒታሊቲ እና በአውሮፕላን ማረፊያዎች አስተዳደር ውጤታማ የገቢ ምንጮችን የገነባው ተቋሙ፤ በአሁኑ ወቅት "ራዕይ 2040"ን ሰንቆ ጉዞውን ቀጥሏል።
አየር መንገዱ መሰረተ ልማት ለዕድገቱ ቁልፍ መሆኑን በመረዳትም፤ በ80 ሚሊየን ዶላር ወጪ ያስገነባውን አዲሱን ዘመናዊ ዋና መስሪያ ቤት በቅርቡ የሚያስመርቅ ይሆናል።
በላሉ ኢታላ