በሀገራችን ተግባራዊ እየተደረገ የሚገኘው የበጀት ፖሊሲ ሥርዓት ከፍተኛ ጥንቃቄ የተሞላበት እና ከብሔራዊ ባንክ ጥብቅ የገንዘብ ፖሊሲና አጠቃላይ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ጋር የተጣጣመ መሆኑን የገንዘብ ፖሊሲ ኮሚቴው አስታውቋል።
በተለይም በ2016 በጀት ዓመት ከተተገበረው ሪፎርም በኋላ መንግሥት የበጀት ጉድለቱን ለመሙላት ከብሔራዊ ባንክ ቀጥታ ብድር እንዳይወስድ መደረጉን የኮሚቴው መግለጫ አስታውሷል።
ይህም የማዕከላዊ ባንኩን የገንዘብ ፖሊሲ አቋም በማገዝ እና የመሠረታዊ ገንዘብ ዕድገትን በመገደብ በኩል ከፍተኛ አስተዋፅዖ አበርክቷል።
በዚህ የተጠናከረ የፖሊሲ እርምጃ ምክንያት የ2018 በጀት ዓመት የመጀመሪያ 10 ወራት አጠቃላይ የበጀት ጉድለት ከጠቅላላ የሀገር ውስጥ ምርት ጋር ያለው ምጣኔ ወደ 0.9 በመቶ ዝቅ ማለቱ ተገልጿል።
ይህ አኃዝ ባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ከነበረው 1.6 በመቶ እንዲሁም ከሪፎርሙ በፊት በ2016 ከተመዘገበው የ2.1 በመቶ ምጣኔ ጋር ሲነፃፀር ጉልህ የሆነ ቅናሽ የታየበት ነው።
ከብሔራዊ ባንክ የሚወሰደው ብድር በመቆሙ መንግሥት የበጀት ጉድለቱን ለመሙላት የመንግሥት ግምጃ ቤት ሰነድ ገበያን በቁልፍ አማራጭነት እየተጠቀመ እንደሚገኝም ነው ኮሚቴው የጠቀሰው።
ይህ የፋይናንስ ሥርዓት ለበጀት አፈፃፀሙም ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ መሆኑን ጠቅሶ፣ በ2018 በጀት ዓመት በዚሁ የመንግሥት ግምጃ ቤት ሰነድ ገበያ አማካኝነት 206.5 ቢሊዮን ብር መሰብሰብ መቻሉን የኮሚቴው መግለጫ አብራርቷል።
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: