Search

17 አደገኛ የሰዎች አዘዋዋሪዎች በቁጥጥር ሥር ዋሉ

ማክሰኞ ሐምሌ 14, 2018 124

 

የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ በምሥራቅ ሀገራችን በኩል በጂቡቲ እና በየመን አድርገው ወደ ሳዑዲ ዓረቢያ ሰዎችን በሕገ ወጥ መንገድ ሲልኩ የቆዩና ከተጎጂዎች ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ የተቀበሉ፣ በአደገኛ ሕገ ወጥ አዘዋዋሪ መሐመድ ጣሂር አደን (ወርዲ) የሚመሩ የተደራጁ 17 የወንጀል ቡድን አባላትን በቁጥጥር ሥር አውሎ የምርመራ መዝገብ በሰውና በሰነድ ማስረጃ በማደራጀት ለፍትሕ ሚኒስቴር መላኩን አስታውቋል።

የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ባሰባሰበው የሰው እና የሰነድ ማስረጃ ተጠርጣሪዎቹ በሰው ልጅ ለመነገድ በማሰብ የወንጀል ቡድን በማደራጀት በወንጀል ድርጊቱ ውስጥ በከፍተኛ ደረጃ መሳተፋቸውን በምርመራ መዝገቡ ማጣራቱን ገልጿል።

ተጠርጣሪዎቹ የሕገ ወጥ የሰዎች ዝውውር መረብ በመዘርጋት፣ ተጎጂዎቹ በየመን በኩል ወደ ሳዑዲ ዓረቢያ ገብተው የተሻለ ኑሮ እንደሚኖሩ ሐሰተኛ ተስፋ በመስጠትና በማሳመን ከተለያዩ የሀገራችን አካባቢዎች በደላሎች አማካኝነት ተጎጂዎችን በመመልመል ሲልኩ መቆየታቸውንም ፖሊስ አረጋግጧል።

በምርመራ መዝገቡ እንደተመለከተው በሕገ ወጥ መንገድ የተወሰዱ ተጎጂዎች የኢትዮጵያን ድንበር እንደተሻገሩ ወደ የመን ተወስደው በየመን ሀገር ውስጥ በሚገኙ ለዚሁ ዓላማ በተዘጋጁ መጋዘኖች ታጉረው ከፍተኛ ኢሰብአዊ ድርጊቶች ይፈጸሙባቸው ነበር።

በተለይም ተጠርጣሪዎቹ ተጎጂዎችን በመያዣነት በመያዝ ወደ ቤተሰቦቻቸው ስልክ በማስደወል ከፍተኛ ገንዘብ ሲጠይቁ እንደነበር እና ገንዘብ መክፈል ላልቻሉ ቤተሰቦች ተጎጂዎችን እየደበደቡ፣ እንዲሁም እያሰቃዩ ቪዲዮ በመቅረጽ የሥነ ልቦና ጫና ሲፈጥሩ እንደነበር ፖሊስ አረጋግጧል።

በዚህም መሠረት የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ከፍትሕ ሚኒስቴር፣ ከብሔራዊ መረጃ እና ደኅንነት አገልግሎት እንዲሁም ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት ባደረገው ጠንካራ ክትትልና ምርመራ በርካታ ከባባድ ግኝቶችን ይፋ አድርጓል።

ከእነዚህም መካከል ሕገ ወጥ አዘዋዋሪዎቹ ከተጎጂዎች 1 ቢሊዮን ብር በላይ በሕገ ወጥ መንገድ መቀበላቸውን፣ 40,000 በላይ ሰዎችን በሕገ ወጥ መንገድ ማዘዋወራቸውን፣ 60 ሰዎች በላይ ለሕልፈተ ሕይወት መዳረጋቸውን፣ እንዲሁም በርካታ ሴቶች መደፈራቸውን በምርመራ ማረጋገጥ ተደርሶበታል።

በዚህ ወንጀል ጉዳይ በርካታ ሰዎች የምስክርነት ቃላቸውን የሰጡ ሲሆን፣ ከሳዑዲ ዓረቢያ እና ከኢትዮጵያ በቀጥታ መስመር በቪዲዮ የምስክርነት ቃላቸውን ሰጥተዋል።

ተጠርጣሪዎቹ በሕገ ወጥ መንገድ ያገኙትን ከፍተኛ ገንዘብ በመጠቀም በሀገር ውስጥ እና በውጭ ሀገር ቋሚና ተንቀሳቃሽ ንብረት ማፍራታቸውን ፖሊስ ያረጋገጠ ሲሆን፣ በስማቸው የነበረ ቤት፣ ተሽከርካሪ እና ገንዘብ እንዲታገድ አድርጓል።

የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ተጠርጣሪዎቹን በሰው የመነገድ፣ በሕገ ወጥ ሐዋላ እና በሕገ ወጥ የገንዘብ ዝውውር (Money Laundering) ወንጀሎች ምርመራውን አጠናቆ ለፍትሕ ሚኒስቴር መላኩን አስታውቋል።

የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ሕገ ወጥ የሰዎች አዘዋዋሪዎችና ተባባሪዎቻቸው በቁጥጥር ሥር እንዲውሉ ድጋፍ ላደረጉ አካላት ምስጋናውን እያቀረበ፤ ኅብረተሰቡ የዜጎች ተሳትፎ መተግበሪያ (EFPApp) 991 ነፃ የስልክ መስመር እና ሰው አልባ ፖሊስ ጣቢያ (SPS) በመጠቀም መረጃ በመስጠት ትብብሩን አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪውን አስተላልፏል።

 

 

አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: