የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ምክር ቤት 6ኛው ዙር 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 10ኛ መደበኛ ጉባኤ በታርጫ ከተማ መካሄድ ጀምሯል።
ጉባኤውን በንግግር የከፈቱት የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ አቶ ወንድሙ ኩርታ፣ ምክር ቤቱ የአሠራር እና የሥነ ምግባር ደንቦችን ይበልጥ ተግባራዊ በማድረግ የድጋፍ እና ክትትል ሥራዎችን አጠናክሮ መቀጠሉን አብራርተዋል።
የምክር ቤቱ ቋሚ ኮሚቴዎችም የአስፈጻሚዎችን ዕቅድ እና ክንውን ክትትል በማድረግ እና ተገቢ የሆኑ ግብረ መልሶችን ተደራሽ በማድረግ ረገድ የተሻለ እንቅስቃሴ እያደረጉ እንደሚገኙም አመላክተዋል።
እንደ ክልል ዘንድሮ ውጤታማ የሆኑ በርካታ የልማት ሥራዎች መሠራታቸውን የገለጹት ዋና አፈ ጉባኤው በግብርና፣ በጤና፣ በትምህርት፣ በፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ፣ በመሶብ አንድ ማዕከላት፣ በሞዴል መንደሮች ግንባታ እና ሌሎችም ዘርፎች ተጨባጭ ውጤቶች ተመዝግበዋል ብለዋል።
የመልካም አስተዳደር ችግሮች ምንጭ የነበሩ ያልተጠናቀቁ መሠረተ ልማቶች ግንባታቸው እንዲጠናቀቁ በማድረግ ለኅብረተሰቡ የልማት ጥያቄዎች ምላሽ በመስጠት እንደ ክልል የተሻለ ተግባር እየተከናወነ እንደሚገኝም አመላክተዋል።
ለሁለት ቀናት የሚካሄደው የምክር ቤቱ ጉባኤ እየተገባደደ ባለው የሥራ ዘመን የተከናወኑ ተግባራትን ጨምሮ የጠቅላይ ፍርድ ቤት እና የዋና ኦዲት መሥሪያ ቤት አፈጻጸም ይገመግማል።
የ2019 ዓ.ም ክልላዊ ረቂቅ የበጀት እና የተለያዩ አዋጆችን መርምሮ እንደሚያጸድቅም ተብራርቷል።
በሰለሞን ባረና
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: