የመደመር መንግሥት ለአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ እንደሚገኝ የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ስዩም መኮንን ገለጹ።
ሚኒስትር ዴኤታው ይህንን ያብራሩት ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ከአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ጋር በመተባበር የ2018 በጀት ዓመት የአካባቢ እና የአየር ንብረት ለውጥ ዘርፍ አፈፃፀም እና የ2019 ዕቅድ ላይ ከክልሎች እና ከከተማ መስተዳድሮች ጋር ባካሄዱት የምክክር መድረክ ላይ ነው።
በአሁኑ ወቅት በዓለም አቀፍ ደረጃ የተከሰተውን የከፋ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ ለመቋቋም ለአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ ቅድሚያ መስጠት ዋነኛው እና ቀዳሚው መፍትሔ መሆኑ ተመላክቷል።
ኢትዮጵያ ለዓለም አቀፉ የካርቦን ልቀት የምታበረክተው አስተዋፅኦ አነስተኛ ቢሆንም፣ ከችግሩ ከፍተኛ ተጋላጭ ሀገራት መካከል እንደምትገኝ ሚኒስትር ዴኤታው ገልጸዋል።
ሀገራችን የችግሩ ሰለባ ብቻ ሳትሆን ተጨባጭ እርምጃዎችን በመውሰድ የመፍትሔው አካል ለመሆን በግንባር ቀደምትነት እየሠራች መሆኑንም አስረድተዋል።
በውይይቱ ወቅት እንደተገለጸው፣ የታዳሽ ኃይል ልማትን ማስፋፋት፣ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን አቅም ማሳደግ፣ የአየር ንብረት ለውጥን የሚቋቋም የግብርና ሥርዓትን ማጠናከር እና የተፈጥሮ አካባቢ ጥበቃ ሥራዎች ለአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ እንደ ዋና መሣሪያ ሆነው በማገልገል ላይ ይገኛሉ።
በተለይም በሀገር አቀፍ ደረጃ በተካሄደው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር በጥቂት ዓመታት ውስጥ ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞች መተከላቸውን አቶ ስዩም አንስተዋል።
ይህም የሀገራችንን የደን ሽፋን በከፍተኛ ደረጃ ከመጨመሩ ባሻገር፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ትልቅ ዕውቅናና አድናቆት ያተረፈ ተግባር መሆኑን አብራርተዋል።
በተጨማሪም ኢትዮጵያ ባለፈው ዓመት 2ኛውን የአፍሪካ የአየር ንብረት ሳምንት ማስተናገዷ እና 32ኛውን የዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ጉባኤ (COP32) እንድታዘጋጅ መመረጧ ሀገራችን ለአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ያላትን ጠንካራ ቁርጠኝነት የሚያሳይ ከመሆኑም በላይ ለተገኘው ውጤታማ ሥራ የተሰጠ ዓለም አቀፋዊ ዕውቅና ማረጋገጫ እንደሆነ ገልጸዋል።
በባዬ ሙላት
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: