ወደ አረንጓዴ ምድር የምታደርገውን ጉዞ በፅናት ያፋጠነችው ኢትዮጵያ፣ በአየር ንብረት ለውጥ ሳቢያ የሚከሰቱ ተፈጥሮአዊ ተጽዕኖዎችን የመቋቋም አቅሟን በተግባር እያረጋገጠች ትገኛለች።
የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር ተራ የዛፍ ተከላ ዘመቻ ሳይሆን፣ የአካባቢ ጥበቃን፣ የምግብ ዋስትናን፣ የማክሮ ኢኮኖሚ እመርታን እና የቀጣናዊ ዲፕሎማሲ የበላይነትን ያጣመረ ሀገር በቀል ስትራቴጂካዊ ተአምር ነው።
ለመሆኑ ይህ መርሐ ግብር ኢትዮጵያን በምን ዓይነት አዲስ የዕድገት ምዕራፍ ውስጥ አስገብቷታል? 10ን ዐበይት የአረንጓዴ ዐሻራ ውጤቶች እንመልከት፡-
ከዕቅድ በላይ የተመዘገበ ግዙፍ የቁጥር እመርታ
በ2011 ዓ.ም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት ሲጀመር የተያዘው እቅድ 4 ቢሊዮን ችግኞችን መትከል የነበረ ቢሆንም፣ በሕዝባዊ ንቅናቄው 4.7 ቢሊዮን ችግኞችን በመትከል ነበር ታሪካዊው ዘመቻ የተከፈተው።
ከዚህ ጠንካራ መነሻ በመነሳትም እስከ 2018 ዓ.ም ባሉት ስምንት ዓመታት ውስጥ ብቻ ወደ 56 ቢሊዮን የሚጠጉ ችግኞችን መሬት በማስያዝ ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ አስደናቂ ተሞክሮ ማበርከት ተችሏል።
በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የተደገፈ የክትትል እና የጽድቅ መጠን ጥራት
የተተከሉት ችግኞች ዝም ብለው የሚተው ሳይሆን በጂኦግራፊያዊ መረጃ ሥርዓት (GIS)፣ በጂፒኤስ (GPS) እና በሳተላይት ምስሎች ታግዘው የሚመሩ በመሆናቸው እያንዳንዱን እድገት ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ መከታተል ተችሏል።
በዚህም ዘመናዊ አሠራር ምክንያት የተተከሉት ችግኞች የመጽደቅ መጠን 84 በመቶ መድረሱ በዳታ ተረጋግጧል።
የዓለምን ትኩረት የሳበው የአንድ ቀን የታሪክ ሪከርድ
ሐምሌ 2018 ዓ.ም በተካሄደው ሀገር አቀፍ ዘመቻ ከ26.2 ሚሊዮን በላይ ዜጎች በአንድ ጀምበር በመሳተፍ በ12 ሰዓታት ውስጥ ብቻ 805.3 ሚሊዮን ችግኞችን ተክለዋል።
ይህ ክንውን በ2017 ዓ.ም ተይዞ የነበረውን የ714 ሚሊዮን ሪከርድ በአዲስ መልክ የሰበረ ታሪካዊ ስኬት ሆኖ ተመዝግቧል።
የሥነ-ምህዳር መታደስ እና የደን ሽፋን ማደግ
በ2011 ዓ.ም 17.2 በመቶ ብቻ የነበረው የኢትዮጵያ የደን ሽፋን፣ ከተሰሩት ግዙፍ አረንጓዴ ስራዎች በኋላ አሁን ላይ ወደ 23.6 በመቶ እና ከዚያ በላይ አድጓል።
ይህም ከ297 ሚሊዮን ቶን በላይ ካርቦን ዳይኦክሳይድ በመምጠጥ ለዓለም አቀፍ የአየር ንብረት መረጋጋት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል።
የመሬት ሀብትን የመጠበቅ እና የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ደኅንነት
ከመርሐ ግብሩ ትግበራ በፊት በየዓመቱ ይሸረሸር የነበረው 1.9 ቢሊዮን ሜትሪክ ቶን አፈር እና ደለል አሁን በተሰራው የተፈጥሮ ጥበቃ ምክንያት ወደ 208 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን ዝቅ እንዲል ተደርጓል።
ይህም የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብን ጨምሮ ሌሎች የውኃ አካላት በደለል ከመሞላት አደጋ የተጠበቁበት ታላቅ ስኬት ነው።
ሰፊ አረንጓዴ የሥራ ዕድል እና የማህበራዊ ፍትሕ ማረጋገጫ
በመላው ኢትዮጵያ ከተቋቋሙት 120 ሺህ በላይ የችግኝ ጣቢያዎች ጋር ተያይዞ ከ1.2 ሚሊዮን በላይ አረንጓዴ የሥራ ዕድሎች ተፈጥረዋል።
ከነዚህ ተጠቃሚዎች መካከል 60 በመቶ የሚሆኑት ሴቶች እና ወጣቶች በመሆናቸው ሥራ አጥነትን በመቀነስ ረገድ የላቀ ማኅበራዊ ፍትሕን አረጋግጧል።
የጥምር ደን ግብርና እና የምግብ ዋስትና እውን መሆን
ከተተከሉት አጠቃላይ ችግኞች መካከል ከ50 በመቶ በላይ የሚሆኑት ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው ተክሎች ናቸው።
አቮካዶ፣ ማንጎ፣ ፓፓያ፣ ፖም፣ ሻይ እና ቡናን የመሳሰሉ ተክሎች በስፋት መተከላቸው የዜጎችን የዕለት ተዕለት ገቢ ከማሳደግ ባለፈ የምግብ ዋስትናን በአስተማማኝ ሁኔታ እያረጋገጠ ነው።
የማክሮ ኢኮኖሚ እመርታ እና የኤክስፖርት ንግድ ዕድገት
በመርሐ ግብሩ የተገኘው ምርት በ2011 ዓ.ም 246 ሺህ ቶን የነበረውን የቡና ኤክስፖርት መጠን በ2017/18 በጀት ዓመት ወደ 469 ሺህ ቶን አሳድጎታል።
በተጨማሪም የፍራፍሬ ምርት በከፍተኛ ሁኔታ መጨመሩ ኢትዮጵያ በአቮካዶ ኤክስፖርት ከአፍሪካ የሁለተኛ ደረጃን እንድትይዝ አስችሏታል።
ሕዝባዊ ባህል እና ብሔራዊ መግባባት
በየዓመቱ ከ25 ሚሊዮን በላይ ዜጎች በነቃ ሁኔታ በዘመቻው ይሳተፋሉ። ይህ ሰፊ ህዝባዊ ጥምረት የአካባቢ ጥበቃን ከመንግስት ፖሊሲነት ባለፈ ወደ ጠንካራ የህዝብ የዘወትር ባህልነት እና ብሔራዊ መግባባት የቀየረ አዲስ ማህበራዊ እሴት ሆኗል።
የረጅም ጊዜ ራዕይ እና የቀጠናዊ ዲፕሎማሲ የበላይነት
ኢትዮጵያ እስከ 2020 ዓ.ም ድረስ 65 ቢሊዮን ችግኞችን ለመትከል ዕቅድ ይዛ እየሠራች ሲሆን፣ ይህም በ2027 ለምታስተናግደው 32ኛው የዓለም አቀፍ የተባበሩት መንግሥታት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ (COP32) ትልቅ ድልድይ ነው።
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: