የመደመር መንግሥት ትኩረት የሰጠው የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርም አካል የሆነው የመንግሥት ሠራተኞችን መረጃ የማሰባሰብ፣ የማጥራት እና ወደ ዲጂታላይዝድ ቋት የማስገባት ሥራ እየተከናወነ ይገኛል።
ይህ አሠራር የተደራጀ የመንግሥት ሠራተኞች መረጃን በመያዝ ፈጣንና ግልጽነት ያለው አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችል ከመሆኑም በላይ፣ የመንግሥትን በጀት ከብክነት ለመታደግ ከፍተኛ ሚና አለው።
በዚህም መሰረት በአማራ ክልል ከሚገኙ ከ500 ሺህ በላይ የመንግሥት ሠራተኞች ውስጥ እስካሁን በነበረው ሂደት የ80 በመቶ ሠራተኞችን መረጃ ማሰባሰብ መቻሉን የክልሉ ሲቪል ሰርቪስ እና የሰው ሀብት ልማት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ወ/ሮ ካሳ አበባው ገልጸዋል።
እንደ ኃላፊዋ ገለጻ፣ በአሁኑ ወቅት የ432 ሺህ በላይ ሰራተኞች መረጃ ተሰብስቦ ወደ ሥርዓቱ ገብቷል።
የመንግሥት ሠራተኛን ትክክለኛ መረጃ በማደራጀት በአንድ ቋት ማስገባት እንደ ሀገር፣ ተቋም እና ግለሰብ ያለው ፋይዳ ከፍተኛ መሆኑን ያነሱት ወ/ሮ ካሳ፤ አሰራሩ በተለይም በሠራተኞች መረጃ ላይ የተመሰረተ ጥቅማጥቅም እና ደሞዝ በትክክል ለመወሰን እንደሚያግዝ ጠቁመዋል።
በክልሉ የተጀመረውን የመረጃ ማሰባሰብ እና የማጥራት ሥራ በወቅቱ ለማጠናቀቅ በየደረጃው በቅንጅት እየተሠራ የሚገኝ ሲሆን፣ የመንግሥት ሠራተኞችም አስፈላጊ መረጃዎቻቸውን በማስመዝገብ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ጥሪ ቀርቧል።
ይህ ሀገራዊ የመረጃ ማሰባሰብ እና የማጥራት ሥራ ከኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት ጋር በመተባበር እየተከናወነ የሚገኝ ነው።
በሳሙኤል ወርቃየሁ
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: