የጋምቤላ ህዝቦች ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ምክር ቤት ለሁለት ቀናት ሲያካሂድ የቆየውን 6ኛ ዙር 5ኛ የስራ ዘመን 10ኛ መደበኛ ጉባኤውን በስኬት አጠናቅቋል።
ምክር ቤቱ በሁለት ቀናት ቆይታው ለክልሉ የ2019 በጀት ዓመት ለልማት እና መልካም አስተዳደር እቅድ ማስፈጸሚያ የሚውል 18 ቢሊዮን 577 ሚሊዮን 523 ሺህ 685 ብር በጀት መርምሮ አጽድቋል።
ጉባኤው በቆይታው የክልሉ የአስፈፃሚ አካላት የ2018 በጀት ዓመት የ12 ወራት የልማት እና የመልካም አስተዳደር እቅድ አፈፃፀም ሪፖርት እንዲሁም የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤትና የዋና ኦዲተር መስሪያ ቤቶችን የሥራ ክንውን ሪፖርቶች በጥልቀት ገምግሟል።
ከዚህ በተጨማሪም ምክር ቤቱ በክልሉ የፍትህ ሥርዓቱን ለማጠናከር የቀረበለትን የ11 ዳኞች ሹመት መርምሮ በማፅደቅ የውሳኔ ሃሳቦችን አጽድቋል።
የምክር ቤቱ ዋና አፈ ጉባኤ ወይዘሮ መሰረት ማቲዎስ በጉባኤው ማጠቃለያ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት፤ በበጀት ዓመቱ የተመዘገቡ አበረታች ስኬቶችን አጠናክሮ ማስቀጠል እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።
አክለውም ያጋጠሙ ክፍተቶችን በማረም በአዲሱ የበጀት ዓመት የተሻለ ውጤትና ፈጣን ልማት ለማስመዝገብ በየደረጃው የሚገኙ አካላት በቅንጅት ሊሰሩ እንደሚገባ አሳስበዋል።
በሚፍታህ አብዱልቃድር
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: