ለሕዝብ መሠረታዊ ጥያቄዎች እውነተኛ ምላሽ ከመስጠት ይልቅ ለጊዜያዊ የፖለቲካ ማክሸፊያ እና ለይስሙላ ፕሮፓጋንዳ ብቻ መሠረት ድንጋይ ተቀምጦላቸው የተተዉ፣ በሐሰተኛ ሪፖርት እና በብልሹ አሠራር የተተበተቡ በርካታ ፕሮጀክቶች ለአያሌ ዓመታት የኢትዮጵያውያንን የልማት ጥማት ሳያረኩ ቆይተዋል።
ተፈጥሮ ሳይሰስትባት እና ጸጋ ሳይጎድላት “ነገን ሳይሆን ዛሬን ብቻ” በሚሉ አፍራሽ ዕሳቤዎች ወደ ኋላ ስትጎተት የኖረችው ሀገራችን፣ ለአላስፈላጊ የፋይናንስ ዕዳ እና ለከፍተኛ የሀብት ብክነት ስትዳረግ መቆየቷ የቅርብ ጊዜ መራራ ትዝታ ነው።
አሁን ግን ይህ ታሪካዊ የልማት ስብራት እና ጠባሳ በመደመር መንግሥት ቁርጠኛ የልማት ውሳኔዎች እና “ለቃል በመታመን” መርሕ ምክንያት ሙሉ በሙሉ እየተሻረ ይገኛል።
የዚህ አዲስ የማስፈጸም አቅም እና የመደመር መንግሥት “የመፍጠር እና የመፍጠን” ዕሳቤ ዋነኛ ማሳያ ሆኖ የሚቀርበው ለ18 ዓመታት በባዶ ተስፋ ሲጓተት የቆየው የመገጭ ግድብ ግንባታ ታሪክ ነው።
ቀደም ሲል በጋ ላይ የተሠራው በክረምት እየተናደ ለአካባቢው አርሶ አደሮች የሕልውና ስጋት፣ ለጣና ሐይቅ ደግሞ የደለል ምንጭ ሆኖ የቆየውን ይህን ግድብ የመደመር መንግሥት ባስቀመጠው ቁርጠኛ አቅጣጫ የመሠረት ችግሮቹን ከመሬት በታች እስከ 35 ሜትር ዘልቆ በመቆፈር በዓለት ላይ እንዲያርፍ አድርጎታል።
በ24 ሰዓት የሥራ ክፍፍል በቀንም በሌሊትም በተደረገው አዲስ አሠራር፣ ባለፉት ሁለት ዓመታት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ አጠቃላይ ግንባታውን 94 በመቶ ማድረስ ተችሏል።
በዚህም ግድቡ 33 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ ውኃ በመያዝ ለደንቢያ አርሶ አደሮች የ17 ሺህ ሄክታር የመስኖ ልማት፣ ለጎንደር ከተማ ደግሞ የዘላቂ መጠጥ ውኃ ብሥራትን ይዞ መጥቷል።
የመደመር መንግሥት ፕሮጀክቶች በየምዕራፉ ተከፋፍለው በተግባር እና በውጤት እንዲለኩ ማድረጉ ከተገኙ ታላላቅ ስኬቶች ጀርባ ያለው ዋና ምሥጢር ነው።
በከፍተኛ ጥራትና ታማኝነት ተጠናቀው የሀገርን ገጽታና የቱሪዝም አቅም የለወጡት የገበታ ለሀገር፣ ለሸገር እና ለትውልድ ፕሮጀክቶች፣ እንዲሁም የከተማና የገጠር ኮሪደር ልማቶች እና የታላቁ ሕዳሴ ግድብ መጠናቀቅ የመደመር መንግሥት ለቃል መታመን የሚከፈልን ዋጋ ያረጋገጠባቸው ድንቅ ማሳያዎች ናቸው።
የመገጭን መሰል ፕሮጀክቶች ከውድቀት እና ከተረሱበት አቧራ መታደግ፣ የሀብት ብክነትን ማስቀረት ብቻ ሳይሆን የሀገርን ክብር እና የሕዝብን እምነት የመመለስ ጉዳይ በመሆኑ፣ በአሁኑ ወቅት የተከተለው የፍጥነት፣ የጥራት እና ለቃል የመታመን ባህል የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ዕድገት እና የትውልድ ቀጣይነት እውን የሚያደርግ አዲስ ሀገራዊ አቅጣጫ ሆኖ ቀጥሏል።
በሰለሞን ገዳ
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: