Search

17 ሺህ ኢትዮጵያውያን የዓይን ብሌናቸውን ለመለገስ ቃል ገብተዋል

ረቡዕ ነሐሴ 14, 2017 148

17 ሺህ ኢትዮጵያውያን ከህልፈት በኋላ የዓይን ብሌናቸውን ለመለገስ ቃል መግባታቸውን የኢትዮጵያ የዓይን ባንክ ገልጿል፡፡

300 ሺህ በላይ የሚሆኑ ሰዎች ደግሞ የዓይን ብሌን ልገሳ እንዲደረግላቸው ተመዝግበው ተራቸውን እየጠበቁ እንደሚገኙም የዓይን ባንኩ ጠቅሷል

ከተመሰረተ 21 ዓመት ያስቆጠረው የኢትዮጵያ የዓይን ባንክ እስካሁን ለ3 ሺህ 600 ሰዎች የዓይን ብሌን ንቅለ ተካላ ማድረጉን የተቋሙ ዋና ሥራ አስፈጻሚ / አምሳለ ጌታቸው ገልጸዋል፡፡

የሕክምና አገልግሎቱን በሚፈለገው ደረጃ መስጠት ያልተቻለባቸው የተለያዩ ምክንያቶች መኖራቸውን ዶ/ር አምሳለ ጌታቸው ከኤፍ ኤም አዲስ 97.1 ካባ መዝናኛ ጋር በነበራቸው ቆይታ አንስተዋል፡፡

በዚህም የለጋሾች ግንዛቤ አነስተኛ መሆን የቴክኒሻኖች እና ቀዶ ሕክምና ባለሞያዎ እጥረት እንዲሁም በለጋሾች እና ድጋፍን በሚፈልጉ ሰዎች መካከል ያለው የቁጥር ልዩን ከፍተኛ መሆን ዋነኛ ምክንያቶች መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡

24 ሰዓት አገልግሎት የሚሰጠው ተቋሙ ማህበረሰቡን በማንቃት ከጊዜ ወደ ጊዜ የተሻለ ለውጥ እያመጣ መሆኑን ጠቅሰው፤ በዚህ ዓመት ሐምሌ ወር ብቻ ለ51 በዓይን ብሌን ጠባሳ ለሚሰቃዩ ሕመምተኞችን የዓይን ብርሃናቸውን መልሰናል ብለዋል፡፡

የዓይን ብሌን ልገሳ የሚካሄደው አንድ ሰው ሕይወቱ ካለፈ እስከ 12 ሰዓት ባለው ጊዜ ውስጥ ሲሆን፣ ግለሰቡ በሕይወት እያለ የዓይን ብሌሉን ለመለገስ ቃል የገባ እና ይሄንንም ለቤተሰቡ ያሳወቀ መሆን ይኖርበታል፡፡

የዓይን ብሌናቸውን መለገስ ወይም ተጨማሪ መረጃ ለመጠየቅ የሚፈልጉ ሰዎች በስልክ ቁጥር 0922726247 ደውለው አገልግሎት ማግኘት እንደሚችሉ  የኢትዮጵያ የዓይን ባንክ ዋና ሥራ አስፈጻሚ / አምሳለ ጌታቸው ተናግረዋል፡፡

በዘነቡ አደም