የመደመር መንግሥት ከንባብ እና ከምርምር ብቻ የተገኘ ሳይሆን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በትልቅ ኃላፊነት ላይ እያሉ ያካበቱትን ተሞክሮ እና ዕውቀት ያካተቱበት መጽሐፍ ነው ሲሉ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፍልስፍና መምህር የሆኑት ዳኛቸው አሰፋ (ዶ/ር) ገለፁ።
መጽሐፉ የሚነበብ ብቻ ሳይሆን ሥራ ላይ የሚውል ሃሳብ እንዳለውም የፍልስፍና መምህሩ አስታውቀዋል።
የመደመር መንግሥት ሰዎች ሊያነቡት የሚገባ የእራሱ የተወሰነ የፍልስፍና ምሰሶዎች ላይ የቆመ መጽሐፍ መሆኑንም ተናግረዋል።
የመጽሐፉ ደራሲ የፖለቲካ ፈፃሚ ብቻ ሳይሆኑ የፖለቲካ አርክቴክትም ናቸው ብለዋል ዳኛቸው አሰፋ (ዶ/ር)።
የፖለቲካ ዘርፉ ላይ የተሰማሩ ሰዎች እንደማጣቀሻ ሊወስዱት የሚገባ ሃሳብን የያዘ መጽሐፍ መሆኑንም አንስተዋል።
መጽሐፉ ከውጭ ከመቅዳት ይልቅ የእራሳችንን አካሄድ መምረጥ ይገባል የሚል ሃሳብ የያዘ እና ከብየና ወደአመክንዮአዊ የሙግት ሽግግር የሚጓዝ ፍሰት እንዳለውም ገልጸዋል።
በተጨማሪ በመጽሐፉ ውስጥ ችግር ናቸው ተብለው የተነሱ ሃሳቦች፤ ችግራቸውን ብቻ ማንሳት ሳይሆን ሌላ የተሻለ ሃሳብን በማስተዋወቅ አንባቢውን መንገድ የሚያመላክቱ መሆናቸውን አስረድተዋል።
መጽሐፉ በርካታ ሃሳቦችን የያዘ ቢሆንም የንብረት ባለቤትነት መብትን የተመለከቱ ጉዳዮችን እንዳላነሳ የገለፁት ዳኛቸው አሰፋ፤ ይህንን ሃሳብ ሌሎችም አንስተው ማንሸራሸር እንዳለባቸውም የፍልስፍና መምህሩ አመላክተዋል።