የባንኮች ውህደት ለግል ባንኮች በርካታ ጥቅሞችን ይዞ ይመጣል ሲሉ የምጣኔ ሀብት ባለሙያው አቶ ዘመዴነህ ንጋቱ ገለጹ፡፡
የባንኮች ውህደት በዋናነት የባንኮቹን የፋይናንስ አቅም ለመሳደግ እንደሚረዳ አቶ ዘመዴነህ ከኤፍ ኤም አዲስ 97.1 ጋር በነበራቸው ቆይታ ተናግረዋል፡፡
የባንኮች ውህደት ሀሳቡ ሲታሰብ ቆየት ማለቱን ያነሱት ባለሙያው፤ የግል ባንኮች በኢትዮጵያ እንዲሰሩ የተፈቀደበት ሁኔታ የ30 አመት ታሪክ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
ይህም ከ30 በላይ ባንኮች እንዲቋቋሙ ምክንያት መሆኑን ነው ያነሱት፡፡
አንዳንድ የግል ባንኮች የፋይናስ አቅማቸው ዝቅተኛ መሆኑ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ለመደገፍ አቅም እንዲያንሳቸው ማድረጉን ጠቅሰዋል፡፡
በአፍሪካ ትልልቅ ባንኮች ዝርዝር ውስጥ 3 የሀገር ውስጥ ባንኮች መገኘታቸውን አንስተው፤ ነገር ግን ደረጃቸው ዝቅ ያለ መሆኑን አመላክተዋል፡፡
ትላልቅ የውጭ ባንኮች ወደ ሀገር ውስጥ መግባት እንዳለባቸውና የባንኮች ውህደት ለባንኮች እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል፡፡
ባንኮች ሲዋሀዱ በፋይናንስ አቅምም ሆነ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ፣ በአዳዲስ አሰራር እና ኢንቨስተሮችን በመሳብ እንደሚጎለብቱ ተናግረዋል፡፡
ብዙ የግል ባንኮች ስጋት ላይ ቢሆኑም ይህ ውህደት ጥቅሙ ላቅ ያለና ወደፊት ለመቀጠል አስፈላጊ ስለመሆኑም ነው የተናገሩት፡፡
በሜሮን ንብረት
#EBC #ebcdotstream #Ethiopia #Foreignbanks