የ117 ዓመቷ ብሪታንያዊት ኤተል ካተርሃም በሕይወት ያሉ የዓለማችን እድሜ ጠገብ ሴት በመሆን አዲስ ታሪካዊ ምዕራፍ ያስመዘገበች ሲሆን፣ የ117ኛ ዓመት ልደቷን በማክበርም ይህንን ዕድሜ ያየች የመጀመሪያዋ ብሪታንያዊት ሴት ሆናለች።
በነሐሴ 1909 በሃምፕሻየር የተወለደችው ካተርሃም፣ በ2025 የብራዚላዊቷ ኢና ካናባሮ ሉካስ ህልፈትን ተከተሎ በሕይወት ያለች የዓለማችን እድሜ ጠገብ ሰው ማዕረግን ተረክባለች።
የልደት በዓሏ በሰሪ በሚገኘው የሙሪያን መንከባከቢያ ማዕከል በደመቀ ሁኔታ የተከበረላት ሲሆን፣ የማዕከሉ ሠራተኞችም ለክብሯ ሲሉ የማዕከሉን አትክልት ስፍራ “የኤተል አትክልት ቦታ” በማለት ሰይመውላታል።
በሰው ልጅ የተመዘገበ ታሪክ ውስጥ ከፍተኛ ዕድሜ ከደረሱ ጥቂት ሰዎች አንዷ የሆነችው ካተርሃም፣ ከ1900 እስከ 1909 ባለው ዘመን ተወልደው በሕይወት ካሉት ሰዎች መካከልም የመጨረሻዋ ናት።
ከአንድ ክፍለ ዘመን በላይ በሚሻገረው ረጅም የሕይወት ጎዳናዋ ሁለቱን የዓለም ጦርነቶች አሳልፋለች፤ ስድስት የብሪታንያ ነገሥታትን ከመመልከቷም በላይ በ110 ዓመቷ ኮቪድ-19ን አሸንፋ በ116ኛ ዓመት ልደቷ በንጉሥ ቻርልስ ሣልሳዊ በአካል ተጎብኝታለች።
በወጣትነቷ በብሪቲሽ ሕንድ በሞግዚትነት የሰራችውና በኋላም ከባሏ ጋር በጊብራልታር እና በሆንግ ኮንግ በመኖር የእንግሊዝኛ ቋንቋ መዋለ ሕፃናት መስርታ የነበረችው ይህች ድንቅ እናት፣ ለአንድ ክፍለ ዘመን ለዘለቀው ረጅም ዕድሜዋ ምስጢሩን ስትጠየቅ “ነገሮችን በረጋ መንፈስ መውሰድ፣ ሰላምን መጠበቅ እና ከማንም ጋር አለመከራከር” እንደሆነ ትመክራለች።
በሲሳይ መንግስቱ
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: