አቶ ኢሳያስ ጅራ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽንን ለተጨማሪ አራት ዓመታት በፕሬዚዳንትነት እንዲመሩ በድጋሚ ተመርጠዋል።
በፌዴሬሽኑ ጠቅላላ ጉባኤ ላይ በተካሄደው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ሂደት፣ ከጠቅላላው 99 አባል ማኅበራትና ክለቦች መካከል 88ቱ የተገኙ ሲሆን፤ 11ዱ በጉባኤው ሳይገኙ ቀርተዋል።
በድምፅ አሰጣጡም ከተገኙት 88 ተወካዮች መካከል 81ዱ ለአቶ ኢሳያስ ጅራ ድጋፋቸውን በመስጠት በከፍተኛ ድምፅ መርጠዋቸዋል።
ከሳምንታት በፊት በተካሄደው የማጣራት ሂደት ብቸኛ ዕጩ ተወዳዳሪ ሆነው የቀረቡት አቶ ኢሳያስ፣ ላለፉት ሁለት የሥልጣን ዘመናት ለስምንት ዓመታት ፌዴሬሽኑን የመሩ ሲሆን፤ የአሁኑን ውጤት ተከትሎም የኢትዮጵያን እግር ኳስ በድምሩ ለ12 ዓመታት በበላይነት የሚመሩ ይሆናል።
ከፕሬዚዳንታዊ ምርጫው በተጨማሪ፣ በቀጣዮቹ ዓመታት ከፕሬዚዳንቱ ጋር በጋራ የሚሰሩ አዳዲስ የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባላትም በፕሬዚዳንቱ ተመርጠው በጉባኤው ይፋዊ ሹመት አግኝተዋል።
በነጻነት ጫንያለው
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: