ኢትዮጵያ በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ ሩብ ዓመት ከውጪ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ከ961 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ አግኝታለች ሲሉ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ዘለቀ ተመስገን (ዶ/ር) ተናግረዋል።
ገቢው ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ከ7 በመቶ በላይ ዕድገት ማሳየቱን ኮሚሽነሩ ለአቢሲ ኤፍ ኤም አዲስ 97.1 በሰጡት መረጃ ገልጸዋል።
በልዩ የኢኮኖሚ ዞኖች ከሚገኙ ኢንቨስትመንቶችም በሩብ ዓመቱ ከወጪ ንግድ ከ49 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ መገኘቱን አክለዋል።
ይህም ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ113 በመቶ ብልጫ አሳይቷል ብለዋል።
በሩብ ዓመቱ ኮሚሽኑ ለ123 የውጭ ባለሀብቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ መስጠቱንም ነው ኮሚሽነሩ የተናገሩት።
ባለፈው ዓመት ለውጭ ባለሀብቶች ክፍት በሆነው በገቢና ወጪ ንግድ ላይም ባለፉት 3 ወራት 34 ባለሃብቶች መሳተፋቸውን አንስተዋል።
ባለሃብቶች የሚያነሷቸውን ቅሬታዎች ለመፍታት እና ኢ-ተገማች የሆኑ የሕግ እና አሠራር ችግሮችን ለመፍታት ከሚመለከታቸው የመንግሥት ተቋማት እና ከክልሎች ጋር በትብብር በመሠራቱ ለውጦች ተመዝግበዋል ብለዋል።
በየተመኙሽ አያሌው
#ebcdotstream #Ethiopia #investment #fdi