የእስራኤል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ሳር ኢትዮጵያ በ2027 ኮፕ32 የአየር ንብረት ኮንፈረንስን እንድታዘጋጅ በመመረጧ የደስታ መልዕክት አስተላልፈዋል።
የእስራኤል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ይህን መልዕክት ያስተላለፉት ከኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ/ር) ጋር በስልክ በተወያዩበት ወቅት ነው፡፡
ሁለቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች የሁለትዮሽ ግንኙነትን አስመልክቶ በመከላከያ፣ በፖሊስ፣ በፈጠራ፣ በልማት እና በሌሎች በጋራ መስራት በሚቻልባቸው ዘርፎች ላይም ተወያይተዋል።
በእስራኤል እና በኢትዮጵያ መካከል ያለውን ታሪካዊ ግንኙነት የበለጠ እያጠናከርን ነው ሲሉም እስራኤል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ሳር መግለጻቸውን በኢትዮጵያ የእስራኤል ኤምባሲ መረጃ ያመላክታል።