ለሁለት ቀናት ይፋዊ የሥራ ጉብኝት ወደ ኢትዮጵያ የመጡት የሕንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ፣ ዛሬ በሕዝብ ተወካዮች እና በፌዴሬሽን ምክር ቤት የጋራ ስብሰባ ላይ ንግግር አድርገዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግራቸውን የጀመሩት “ዛሬ እዚህ ፊታችሁ ስቆም በታላቅ ክብር ነው፤ “የአንበሶቹ ምድር በሆነችው በታላቋ ኢትዮጵያ መገኘት እጅግ ታላቅ የደስታ ስሜት የሚሰጥ ነው፤ እኔ የተወለድሁባት የሕንዷ ጉጅራትም የአንበሶች ቤት ናት፤ ዛሬ እዚህ መገኘቴ ልክ ቤቴ እንደተገኘሁ ያህል ነው” በማለት ነው።
የጥንታዊ እውቀት ባለቤት እና የዘመናዊነት ሕልም ያለው ሕዝብ ማዕከል በሆነው በዚህ የዴሞክራሲ ቤት ውስጥ መገኘትም ታላቅ ክብር ነው ብለዋል።
በ1.5 ቢሊዮን በላይ በሚሆነው የሕንድ ሕዝብ ስም የወዳጅነት ሰላምታ፣ መልካም ምኞት እና ወንድማማችነትን ይዘው ስለመምጣታቸውም ተናግረዋል።
በዚህ ታላቅ ምክር ቤት ውስጥ ሕጎቻችሁ ይወጣሉ፤ እዚህ ውስጥ የሕዝቡ መሻት የመንግሥት መሻት ይሆናል፤ የመንግሥት መሻት ከሕዝብ መሻት ጋር ሲጣጣም ደግሞ የፕሮግራሞች መሻት ከተስፋ እና ከዓላማ ጋር ወደ ፊት ይጓዛሉ ብለዋል።
ዛሬ ፊታችሁ ቆሜ በእናንተ በኩል የምናገረው በየእርሻ ሜዳ ላሉ አርሶ አደሮቻችሁ፣ አዳዲስ ሐሳቦችን ለሚያፈልቁ የሥራ ፈጣሪዎች፣ ተቋማትን እና ማኅበረሰብን ለሚመሩ ጠንካራ ሴቶች እንዲሁም የኢትዮጵያን መፃኢ ጊዜ ለሚቀርፁ ወጣቶች ጭምር ነው ሲሉም ተናግረዋል።
ትናንት ለተደረገላቸው የክብር አቀባበል በእጅጉ አመስግነዋል።
“ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኢትዮጵያ ታላቁ ክብር የሆነውን የክብር ኒሻን ስላበረከቱልኝም እጅግ አመሰግናለሁ! ይህንን ክብር በታላቅ ትህትና እጄን አጣጥፌ በሕንድ ሕዝብ ስም ተቀብያለሁ ‘አመሰግናለሁ'" ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ።
ኢትዮጵያ በሰው ልጆች ታሪክ ውስጥ ጥንታዊ ሥልጣኔዎች አንዷ ናት ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ፣ በዚህ ሀገር ታሪክ ተራራዎች ላይ፣ በሸለቆዎች ውስጥ አና በኢትዮጵያውን ልብ ውስጥ ተጽፎ ተቀምጧል ሲሉ ተናግረዋል።
በዮናስ በድሉ
#EBC #ebcdotstream #Ethiopia #India #PMAbiy #NarendraModi