በኢትዮጵያ በንግድ እና ኢንቨስትመንት ላይ የተሰማሩት ሕንዳዊው ካውሻል ሻሺካንት ከኢቢሲ ጋር ባደረጉት ቆይታ፥ የኢትዮጵያ እና የሕንድ ግንኙኘት የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት ነው ሲሉ ገልጸዋል።
የጋንዲ ሆስፒታል መስራች የልጅ ልጅ የሆኑት እና አማርኛን አቀላጥፈው የሚናገሩት ካውሻል ሻሺካንት፥ የኢትዮጵያ እና የሕንድ ግንኙነት የሺህ ዘመናት ታሪክ ያስቆጠረ መሆኑን ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ እና ሕንድ ከጥንት ጀምሮ የንግድ ግንኙነት እንደነበራቸው ጠቅሰው፤ አሁንም በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለው የኢኮኖሚ ትስስር ጠንካራ መሆኑን ገልጸዋል።
በአሁኑ ወቅት በርካታ ሕንዳውያን ባለሀብቶች በኢትዮጵያ በኢንቨስትመንት በመሳተፍ ላይ እንደሚገኙም አክለዋል።
ዓለም በሞላ አንድ መንደር በሆነበት በዚህ ወቅት በትብብር በመሥራት ዕድገትን ማፋጠን ግዴታ መሆኑን ጠቁመው፤ ሕንድ እና ኢትዮጵያም ያላቸውን አቅም በማስተባበር በጋራ ሠርተው በጋራ ማደግ ይገባቸዋል ብለዋል።
ኢትዮጵያ እና ሕንድ ሁለቱም አዳጊ ሀገራት በመሆናቸው በተለያዩ ዘርፎች የእርስ በርስ የልምድ ልውውጥ በማድረግ በትብብር ቢሠሩ ዕድገታቸውን ለማፋጠን እንደሚያስችላቸውም ነው የገለጹት።
በንፍታሌም እንግዳወርቅ
#EBCdotstream #Ethiopia #India