የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ዛሬ ማለዳ 16 ሺህ ሴቶች የተሳተፉበትን የ5 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ በድምቀት አስጀምረዋል።
በታላቁ ሩጫ አዘጋጅነት በየዓመቱ የሚካሄደው ይህ ውድድር፤ ዘንድሮ በኮሪደር ልማት አዲስ መልክ ባገኘውና ምቹ በሆነው በቦሌ - አትላስ - ኡራኤል መንገድ ላይ ተከናውኗል።
ከንቲባዋ በውድድሩ መክፈቻ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት "ሴቶች በጥበብ ይኖራሉ፤ በራስ መተማመን ይሠራሉ፤ በራስ መተማመን ይሮጣሉ፤ ይችላሉም!" በማለት የሴቶችን አቅምና ተሳትፎ አድንቀዋል።
አክለውም ሁሉም ሴቶች እጅ ለእጅ ተያይዘው የሀገሪቱን ብልፅግና ለማረጋገጥ እንደሚሰሩ ያላቸውን እምነት ገልጸዋል።
በመጨረሻም ውድድሩን ላጠናቀቁ ተሳታፊዎች በሙሉ "ሁላችሁም አሸናፊዎች ናችሁ" በማለት የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል።