ኢትዮጵያ ከስንዴ እርዳታ ተላቅቃ ይልቁንም ስንዴን አምርታ ለውጭ ገበያ ለማቅረብ እየሠራች ትገኛለች።
ባለፉት ስምንት የለውጥ ዓመታት የኢትዮጵያ የእርዳታ ጥገኝነት ታሪክ ተቀይሮ በአፍሪካ ከፍተኛ ስንዴ አምራች ሀገር ለመሆን በቅታለች።
ለውጡ ታዲያ በአጋጣሚ የመጣ ሳይሆን የጥበብ እና የስትራቴጂ ውጤት ነው።

ከባህላዊ የአስተራረስ ዘዴ ወደ ሜካናይዜሽን የተደረገው ሽግግር የኢትዮጵያን አርሶ አደር የገበያ መሪ አድርጎታል።
የሀገራችን አርሶ አደር አሁን ዝናብን ከሰማይ መጠበቅ አቁሞ፣ ሰው ሰራሽ ወንዞችን እንዲሁም መስኖን በመጠቀም ምድሪቱን አረንጓዴ ምንጣፍ በማልበስ ላይ ይገኛል።
በዚህም ኢትዮጵያ ስንዴን በስፋት በማምረት፣ ለዘመናት ያስጎነበሳትን የእርዳታ ቀንበር መስበር ችላለች።
አንድ ሀገር ራሱን መመገብ ችሎ ሲገኝ፣ በዓለም አቀፍ መድረክ የሚኖረው ተቀባይነት እና ተደማጭነት ይጨምራል።
የምግብ ሉዓላዊነት በምግብ ራስን ከመቻል ባሻገር፣ ያለማንም ጫና የግብርና ፖሊሲን መተግበር መቻል ማለት ነው።
በግብርናው ዘርፍ የነበሩ የአስተሳሰብ ድክመቶችን ከመቅረፍ ጀምሮ በተለይ በብልጽግና መንግሥት የተተገበረው የኢኮኖሚ ማሻሻያ ለዘርፉ መሻሻል አዲስ ምዕራፍ ከፍቷል።
በዚህም ባለፉት ስምንት የለውጥ ዓመታት በስንዴ ልማት የተከናወነው ተግባር ደማቅ ስኬት ሆኖ ተመዝግቧል።

ከዚያ ቀደም ኢትዮጵያ የስንዴ ምርትን ከውጭ ለማስገባት በዓመት 1 ቢሊዮን ዶላር ታወጣ ነበር። ያን ያህል የውጭ ምንዛሬ ያስወጣ የነበረው ስንዴ ዛሬ በሀገር ውስጥ ምርት ተተክቷል።
ከዚህም ባለፈ በ2015 ዓ.ም ሀገራችን ለመጀመሪያ ጊዜ ስንዴን ወደ ውጭ የላከችበት አጋጣሚ፣ ዓለም በአግራሞት እንዲመለከተን ያደረገ ትልቅ ስኬት ነበር።
በ2010 ዓ.ም በኢትዮጵያ የእርሻ መሬቶች ላይ ይሠሩ የነበሩ ትራክተሮች ቁጥር 4 ሺህ 716 ብቻ ነበር።
ዛሬ ይህ ቁጥር በከፍተኛ መጠን አድጎ ከ27 ሺህ በላይ ብረት ለበስ ትራክተሮች በእርሻ መሬቶቻችን ላይ እየሠሩ ይገኛሉ። በተመሳሳይ የኮምባይነሮች ቁጥር ከ338 ተነስቶ ከ8 ሺህ በላይ ደርሷል።

ዓመታዊ የስንዴ ምርት መጠንም ከ231 ሚሊዮን ኩንታል በላይ በመድረሱ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎቻችን ከእርዳታ ጠባቂነት ተላቅቀዋል።
የግብርና ዘርፍ ዕድገት በ2010 ዓ.ም ከነበረበት 1.3 በመቶ ተነስቶ በ2017 ዓ.ም 2.3 በመቶ መድረሱም፤ ኢትዮጵያ የእርዳታ ጥገኝነት ቀንበርን ሰብራ ራሷን የቻለች፣ የበለጸገች ሀገር ለመሆን የያዘችውን ግብ ለማሳካት ትልቅ እገዛ እያደረገ ነው።
ይህ ስኬት ለኢትዮጵያ ከቁጥሮች በላይ ዋጋ ያለው ነው፤ በ2018 ዓ.ም የሀገራችንን የኢኮኖሚ ዕድገት ወደ 10.3 በመቶ ከፍ ለማድረግ በሞተርነት እያገለገለ ይገኛል።
ኢትዮጵያ በስንዴ ልማት ያስመዘገበችውን ድል፣ ዛሬ ላይ በሩዝ፣ በአትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም በሌማት ትሩፋት እየደገመችው ትገኛለች።
በንፍታሌም እንዳወርቅ
#Ethiopia #wheat #successstory #EBC