በአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ዛሬ የተመረቀው እና ሥራውን በይፋ የጀመረው ሁለገብ የገበያ ማዕከሉ በአዲስ አበባ የነዋሪዎችን የኑሮ ጫና ለማቅለል የተከፈተ 7ኛው የገበያ ማዕከል ነው።
የገበያ ማዕከሉ የሰብልና ጥራጥሬ እንዲሁም የአትክልትና ፍራፍሬን ጨምሮ የፍጆታ ምርቶች በቅናሽ ዋጋ የሚቀርቡበት እንዲሁም አምራቾች ያለ ደላላ ለሸማቾች ምርት የሚያቀርቡበት ነው።
ማዕከሉ የኑሮ ጫናን ለማቅለል ትልቅ አስተዋፅኦ ያደርጋል ያሉት ከንቲባ አዳነች፣ በመዲናዋ የሕዝቡን የኑሮ ጫና የሚቀንሱ በርካታ ሥራዎች በማከናወን በሰው ሕይወት ላይ ለውጥ የሚያመጣ ሰው ተኮር ልማት መሥራት የመንግሥታችን መለያ ተግባር ሆኗል ብለዋል።
ኑሮን ማቅለል የምንችለው ምርትና ምርታማነትን በማሳደግና የግብይት ሰንሰለቱን በማስተካከል ነው ያሉት ከንቲባዋ፣ ሁሉም ነገር በተሟላለት በዚህ የገበያ ማዕከል ምርቶች በቅናሽ እንዲሸጡ ከ200 ሚሊዮን ብር በላይ ድጎማ መደረጉን ገልጸዋል።
በአዲስ አበባ የምርት አቅርቦትን ለማሳለጥ በከተማዋ በሮች ላይ ከዚህ ቀደም 6 የገበያ ማዕከላት መከፈታቸው እንዲሁም የቅዳሜ እና እሁድ ገበያዎች መስፋፋታቸው የነዋሪዎችን የኑሮ ጫና ለማቅለል ከፍተኛ አስተዋፅኦ እንደሚያበረክት ተናግረዋል።
በይመር አደም
#AddisAbaba #Lemi #MarketCenter #EBC