የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) በክልሉ ምክር ቤት 6ኛ ዙር 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 10ኛ መደበኛ ጉባዔ ላይ ሪፖርት አቅርበዋል፡፡
በሪፖርታቸው መንግሥት በበደሎች እና ቁርሾዎች ላይ እርቅን በማውረድ ዘላቂ ሰላም እና የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ዐበይት ተግባራትን ማከናወኑን ገልጸዋል።
በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት በክልሉ በተከናወኑ የኢኮኖሚና ግብርና ሥራዎች ከ23.2 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የምርት መጠን የተሰበሰበ ሲሆን፣ ከ61 ሺህ ቶን በላይ ቡና ለማዕከላዊ ገበያ ቀርቧል።
በማዕድን ዘርፉም ከ348 ኪሎ ግራም በላይ ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ ገቢ መደረጉን እንዲሁም ከፍተኛ መጠን ያለው የድንጋይ ከሰልና የኮንስትራክሽን ማዕድን መመረቱን ርዕሰ መስተዳድሩ አብራርተዋል።
በማኅበራዊ ዘርፍ “ትምህርት ለትውልድ” ንቅናቄ በተሰበሰበ 832 ሚሊዮን ብር 45 ሞዴል ቅድመ-አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተገንብተው ለአገልግሎት በቅተዋል።
በተጨማሪም የንጹህ መጠጥ ውኃ ሽፋን 44 በመቶ መድረሱ እና የዲጂታል አቅምን ለማሳደግ ከ43 ሺህ በላይ ዜጎች በ"5 ሚሊዮን ኢትዮ ኮደርስ" የሥልጠና ማረጋገጫ ማግኘታቸው በሪፖርቱ ተመላክቷል።
ቀልጣፋ የመንግሥት አገልግሎትን ለማስፋፋትም በልዩ ልዩ የክልሉ ከተሞች ስድስት የ"መሶብ" ማዕከላት ተመርቀዋል።
ክልሉ በበጀት ዓመቱ ከ18.2 ቢሊዮን ብር በላይ የውስጥ ገቢ በመሰብሰብ 64 በመቶ የበጀት ፍላጎቱን በራሱ አቅም መሸፈን መቻሉን የገለጹት ርዕሰ መስተዳድሩ፣ በአሁኑ ወቅት የምክር ቤቱ አባላት ባቀረቡት በዚህ ዝርዝር ሪፖርት ላይ ሰፊ ውይይት እያደረጉ እንደሚገኙ ታውቋል።
በሰለሞን በረና
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: