የገንዘብ ሚኒስቴርና ተጠሪ ተቋማት የ2018 በጀት ዓመት ዋና ዋና የኢኮኖሚና የፋይናንስ አፈጻጸማቸውን በመገምገም፣ በ2019 ዕቅዶችና የትኩረት አቅጣጫዎች ዙሪያ ውይይት አካሂደዋል።
መድረኩን የመሩት የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሺዴ፣ የ2018 የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ አፈጻጸም እጅግ ውጤታማ እንደነበር ገልጸው፤ በተለይም የዋጋ ንረትን በመቆጣጠር፣ የሀገር ውስጥ ገቢን በማሳደግና ከልማት አጋሮች ጋር የሚደረገውን ትብብር በማጠናከር በኩል ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን አብራርተዋል።
በተጨማሪም ከዓለም አቀፍ አበዳሪ አካላት ጋር በተደረገው የዕዳ ሽግሽግ ስምምነት መሠረት ክፍያ መፈጸም የተጀመረበት ስኬታማ ዓመት እንደነበር ጠቁመዋል።
የ2019 በጀት ዓመትን በተመለከተም የተጀመረውን የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ አጠናክሮ በመቀጠል፤ የጸደቀውን በጀት በተሟላ መልኩ ማሳካት እና የሀገር ውስጥ ገቢን ማሳደግ ላይ ልዩ ትኩረት እንደሚደረግ ሚኒስትሩ አቅጣጫ አስቀምጠዋል።
የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ፍቃዱ ሆረታ በበኩላቸው፤ ሚኒስቴሩ የሚሰጣቸውን አገልግሎቶች ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ ለማድረግ በርካታ ተግባራት መከናወናቸውን ጠቅሰው፣ ከማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርሙ ጎን ለጎን የተጀመሩ ተቋማዊ የሪፎርም ሥራዎች በዘንድሮው በጀት ዓመትም ትልቅ ትኩረት እንደሚሰጣቸው ገልጸዋል።
በመጨረሻም ከተሳታፊዎች ለተነሱ ጥያቄዎችና አስተያየቶች በሚመለከታቸው አመራሮች ማብራሪያ ተሰጥቶ ውይይቱ ተጠናቋል።
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: