ኢትዮጵያ ከቻይና ጋር ያላት የኢኮኖሚ ትብብር ከቡና ንግድ ባለፈ እሴት በተጨመረባቸው ምርቶች እና በኢንዱስትሪ ትስስር ላይ እንዲያተኩር በትኩረት እየተሠራ መሆኑን የኢፌዲሪ ፕሬዚዳንት ታየ አጽቀሥላሴ ተናገሩ።
ፕሬዚዳንቱ በቻይና-ኢትዮጵያ የኢኮኖሚና የቡና ንግድ ማስተዋወቂያ ኮንፈረንስ ላይ እንደገለጹት፤ የኢትዮጵያ እና የቻይና የማይበገር ስትራቴጂካዊ አጋርነት ወደ ላቀ የኢንዱስትሪ ሽግግር እንዲያመራ በትብብር ይሠራል።
ትብብሩ በግብርና፣ በአረንጓዴ ልማት እና በቀጥተኛ የውጭ ኢንቨስትመንት ላይ ትኩረቱን በማድረግ የኢትዮጵያን የኢንዱስትሪ ሽግግር ለማፋጠን ያለመ መሆኑንም ፕሬዚዳንቱ አመላክተዋል።
በተለይም የቻይና ከተሞች ያላቸውን የኢንዱስትሪ አቅም ከኢትዮጵያ የልማት ፍላጎት ጋር በማጣመር ዘላቂ የኢኮኖሚ ሥርዓት ለመፍጠር የታለመ ስትራቴጂካዊ ዕቅድ መኖሩን አስታውቀዋል።
ይህ ዓይነቱ ትብብር ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ የንግድ ሰንሰለት ውስጥ ትርጉም ያለው ተሳትፎ እንዲኖራት የሚያስችል መሆኑን ፕሬዚዳንት ታየ አጽቀሥላሴ ጠቁመዋል።
በቻይና-አፍሪካ ትብብር ማዕቀፍ ውስጥ፤ ግብርና እና ገጠር-ተኮር አረንጓዴ ልማት፣ ንግድ፣ ቀጥተኛ የውጭ ኢንቨስትመንት እና የትራንስፖርት ትስስር ወደ ሰፊ የኢንዱስትሪ ሽግግር የሚያደርሱ መንገዶች እንዲሆኑ የጋራ ራዕይ መሰነቁን አክለው ገልጸዋል።