Search

አጠቃላይ ተቀማጩን ከ2 ትሪሊዮን ብር በላይ ያደረሰው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ

ሓሙስ ታኅሣሥ 23, 2018 166

የባንኩ የማኔጅመንት አባላት በተሰበሰቡበት ዛሬ ይፋ በተደረገው መረጃ መሠረት፥ ባንኩ በ2025/26 በጀት ዓመት የመጀመሪያ አጋማሽ ብቻ 325 ቢሊዮን ብር በላይ ተጨማሪ ተቀማጭ በመሰብሰብ አጠቃላይ ተቀማጩን 2 ትሪሊዮን ብር አድርሷል።

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፕሬዚዳንት ተወካይ እና የኮርፖሬት አገልግሎቶች ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ኤፍሬም መኩሪያ፥ ባንኩ 3 ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ አጠቃላይ ተቀማጩን በእጥፍ በማሳደግ 2 ትሪሊዮን ብር ማድረሱን ተናግረዋል።

አቶ ኤፍሬም፥ አፈፃፀሙ 2030 የባንኩ ስትራቴጂ ውጤት መሆኑን እና ይህም ለባንኩ ትልቅ ስኬት መሆኑን በመግለፅ፤ ለስኬቱ መገኘት ከፍተኛ አስተዋፅኦ የነበራቸውን ሪጅኖች፣ ዲቪዥኖች፣ ዲስትሪክቶች እንዲሁም መላውን ሠራተኛ እና ደንበኞችን ጭምር አመስግነዋል።

ስኬቱ በቀጣዮቹ 6 ወራትም የተሻለ ለመሥራት እንደሚያነሳሳ እና በበጀት ዓመቱ መጨረሻ 750 ቢሊዮን ብር አጠቃላይ ተቀማጭ ለማሰባሰብ ታልሞ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል።

ለዚህም ሁሉም የባንኩ ማኔጅመንትና ሠራተኞች፣ የነበሩ ድክመቶችን በማረምና ጠንካራ ጎኖችን በማስቀጠል እንዲሠሩ አቶ ኤፍሬም አሳስበዋል።

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የቢዝነስ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ደረጀ ፉፋ በበኩላቸው፥ ባንኩ 34 ወራት ውስጥ የትሪሊዮን ብስራትን መድገሙን አስታውሰው፤ ከባንኩ ሪጅኖች እስከ ቅርንጫፎች ለዚህ ስኬት ለመብቃት በርካታ ውጣ ውረዶች መታለፋቸውን ጠቁመዋል።

አቶ ደረጀ አክለውም፥ በበጀት ዓመቱ 6 ወራት ብቻ የተገኘው ተቀማጭ ገንዘብ፣ በየወቅቱ አቅማችንን በእጥፍ እያሳደግን ለመምጣታችን ማሳያ ነው ብለዋል።

ከዚህ የላቀ ስኬት ለማምጣት ሁሉም በጋራ እንዲሠራም የሥራ ሃላፊዎቹ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።

#EBC #ebcdotstream #CBE