Search

በቢሾፍቱ አውሮፕላን ማረፊያ ፕሮጀክት የሚሳተፉ የዓለማችን ታዋቂ ኩባንያዎች

ሰኞ ጥር 04, 2018 58

ከትናንት በስቲያ ግንባታው በይፋ የጀመረው የቢሾፍቱ አውሮፕላን ማረፊያ ፕሮጀክት ከህንጻ ዲዛይን ጀምሮ የፕሮጀክቱ አማካሪና ተቆጣጣሪ በመሆን የሚሠሩት በሥነ-ሕንጻ ስመ ጥር የሆኑ ግዙፍ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች ናቸው።

ከዓለማችን ትላልቅ አውሮፕላን ማረፊያዎች አንዱ በሆነው እና በአፍሪካ ተወዳዳሪ በሌለው የቢሾፍቱ አውሮፕላን ማረፊያ ፕሮጀክት ግንባታ ከሚሳተፉ ኩባንያዎች መካከል ዛሃ ሃዲድ እና ፓስካል ዋትሰን በዲዛይን እና መሰል ሥራዎች የተሳተፉ ሲሆን፤ ፕሮጀክቱን የማማከር እና የመቆጣጠር ሥራው ደግሞ ዳር አል-ሃንዳሳ በተባለ የኮንስትራክሽን ኩባንያ የሚመራ ይሆናል።

ከተመሠረተ 70 ዓመታትን ያስቆጠረው ዳረል-ሃንዳሳ ኩባንያ በ60 ሀገራት ውስጥ ከ9 ሺህ 250 በላይ ሠራተኞች ያሉት ግዙፍ ድርጅት ሲሆን፤ በ70 ዓመታት ታሪኩ የ540 ቢሊዮን ዶላር ዋጋ ያላቸው ከ4 ሺህ 500 በላይ ፕሮጀክቶችን ማከናወን የቻለ ኩባንያ ነው።

በኢትዮጵያም ከወራት በፊት ግንባታው የተጀመረው በርዝመቱ በአፍሪካ ተወዳዳሪ የሌለውን የኢትዮጵያ ኤሌትሪክ አገልግሎት ሕንጻ ግንባታን የማማከርና የመቆጣጠር ሥራ የያዘው ይህ ግዙፍ ድርጅት ነው።

በቢሾፍቱ አውሮፕላን ማረፊያ ፕሮጀክት ዲዛይንና መሰል ስራዎች ላይ የተሳተፈው ሌላው ታዋቂ ኩባንያ ዛሃ ሃዲድ አርክቴክትስ ነው።

ድርጅቱ እአአ በ1980 የተመሠረተ ሲሆን፤ በ44 ሀገራት በመቶዎች የሚቆጠሩ ልዩ እና ዘመናዊ ዲዛይን ያላቸው ፕሮጀክቶችን በማከናወን የተሳካለት ኩባንያ መሆኑን አስመስክሯል።

በሥነ-ሕንጻ ጥበባቸው የረቀቀ ውበትን የተላበሱ ዘመናዊ ሕንጻዎችን በመገንባት የታወቀው ይህ ኩባንያ በ25 ዓመት የሥራ ዘመኑ ከዓለማችን ትላልቅ የአውሮፕላን ማረፊያዎች መካከል የሚመደበውን የቻይና ቤይጂንግ ዳግሲንግ አውሮፕላን ማረፊያ ሕንጻን፣ የአዘርባጃኑን ሄይዳር አሊዬቭ ሴንተር፣ በቻይና ጉዋንዡ የሚገኘውን የኦፔራ ማዕከል እና በጣልያን ሮም የሚገኘውን የማክሲ ሙዚየምን ጨምሮ በመቶዎች የሚቆጠሩ ፕሮጀክቶችን አጠናቆ ያስረከበ ስኬታማ የኮንስትራክሽን ኩባንያ ነው።

ሌላኛው ከዛሃ ሃዲድ ጋር በመሆን የአዲሱን አውሮፕላን ማረፊያ የግንባታ ንድፍ የሠራው ኩባንያ ዋና መሥሪያ ቤቱን በኢንግላንድ ያደረገው ፓስካል ዋትሰን ነው። 

የ70 ዓመታት የካበተ ልምድ ያለው ይህ የኮንስትራክሽን ኩባንያ በአየርላንድ የሚገኘውን የዳብሊን አውሮፕላን ማረፊያ፣ በሳውዲ ሪያድ የሚገኘውን የንጉሥ አብዱልአዚዝ አውሮፕላን ማረፊያ እና የሪያድ የሜትሮ ባቡር መስመር ግንባታን ጨምሮ በርካታ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን ያከናወነ ነው።

በዋሲሁን ተስፋዬ

#EBCDotstream #Ethiopia #BishoftuInternationalAirport #ZahaHadid #PascallWatson #daralhandasah