ኢትዮጵያ በአስር ዓመቱ የግብርና መሪ ዕቅድ ውስጥ በትኩረት እንዲሰራባቸው ካስቀመጠቻቸው ስትራቴጂካዊ ዘርፎች መካከል አንዱ የሆነው የግብርና ኢንቨስትመንት የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥ፣ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ የመተካት እና የውጪ ምንዛሪን የማሳደግ ሀገራዊ ግቦችን በላቀ ስኬት እያሳካ ይገኛል።
የሀገራችንን ሰፊ የግብርና አቅም በመጠቀም በርካታ የሀገር ውስጥና የውጭ ባለሃብቶች በስፋት ተሰማርተው ወደ ልማት ገብተዋል።
በአሁኑ ወቅት በሀገር አቀፍ ደረጃ በእርሻ ኢንቨስትመንት ብቻ ከ2 ነጥብ 3 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በ8 ሺህ 904 ባለሀብቶች እጅ ላይ እንደሚገኝ የግብርና ሚኒስቴር መረጃ ያመላክታል።
መንግሥት ይህንን ዘርፍ ይበልጥ ለማሳደግ በመሬት አቅርቦት፣ የፋይናንስ አገልግሎትን ተደራሽ በማድረግ፣ በውል እርሻ እና በመሰረተ-ልማት ማመቻቸት ረገድ በርካታ ስራዎችን እያከናወነ ይገኛል።
ከዚህ በተጨማሪም የግብርናውን ዘርፍ ሽግግር የሚያፋጥኑ የሀገር በቀል ቴክኖሎጂዎችን ለባለሀብቶች የማስተዋወቅ ስራ በትኩረት እየተከናወነ ሲሆን ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ በተተገበሩ ዘመናዊ አሰራሮች፣ በኮንትራት እርሻ፣ በምርጥ ዘር ብዜት እንዲሁም በአካታች የሕግ ማዕቀፎች ምክንያት አመርቂ ውጤቶች እየተመዘገቡ ነው።
በአሁኑ ወቅት አበባ፣ አትክልት፣ ፍራፍሬ፣ ሰብል እና እንስሳት በኢንቨስትመንት ደረጃ በስፋት እየለሙ ለሀገር ውስጥ ፍጆታና ለወጪ ንግድ በከፍተኛ ደረጃ እየቀረቡ ይገኛሉ።
ለአብነትም የአበባ፣ የአትክልት እና የፍራፍሬ የወጪ ንግድ አፈፃፀምን ስንመለከት በ2013 ዓ.ም ከ309 ሺህ 866 ነጥብ 8 ቶን ምርት 531 ሺህ 480 ዶላር ተገኝቷል።
ይህ ቁጥር በ2017 ዓ.ም እጅግ ከፍተኛ ዕድገት በማሳየት ከተላከው 395 ሺህ 911 ነጥብ 9 ቶን ምርት 670 ሺህ 627 ነጥብ 4 ዶላር ገቢ ለማግኘት ተችሏል።
የዘንድሮውን የ10 ወራት አፈፃፀም ስንመለከት ደግሞ ከ236 ሺህ 415 ነጥብ 3 ቶን ምርት 408 ነጥብ 2 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘት መቻሉን የሚኒስቴሩ መረጃ ያረጋግጣል።
በሌላ በኩል ለሀገራዊ ኢኮኖሚ፣ ለስራ እድል ፈጠራ እና ለእውቀት ሽግግር ከፍተኛ አስተዋፅዖ ያለው የእንስሳት ኢንቨስትመንትም ሌላው ትኩረት የተሰጠው ዘርፍ ነው።