የኢትዮጵያ መንግሥት ላለፉት ዓመታት ሲተገብረው የቆየው ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርም፣ ሀገራችንን ከአሳሪ የፖለቲካል ኢኮኖሚ በማላቀቅ ወደ ተረጋጋ የማክሮ-ኢኮኖሚ ምህዳር እያሸጋገራት ይገኛል። የ2018 በጀት ዓመት የዘጠኝ ወራት አፈጻጸም ሪፖርት እንደሚያሳየው፣ ኢኮኖሚው ካጋጠሙት ዓለም አቀፋዊና ሀገራዊ ፈተናዎች አገግሞ መዋቅራዊ ለውጥ ወደአመጣ ጥራት ያለው ዕድገት ተሻግሯል። ይህ ስኬት ዝም ብሎ የመጣ ሳይሆን፣ መዋቅራዊ ስብራቶችን ለመጠገን የተወሰዱ ደፋር የፖሊሲ እርምጃዎችና አዲስ የፖለቲካ ኢኮኖሚ እይታ የወለዷቸው ተግባራዊ ውጤቶች ናቸው።
የፊስካል ጤናማነት እና ጤናማ የመንግሥት ዕዳ
የሪፎርሙ ትልቁ ስኬት የሚለካው መንግሥት የፋይናንስ አስተዳደሩን ከነበረበት የዕዳ ጫና ማላቀቅ መቻሉ ላይ ነው። የመንግሥት ገቢ ወጪን የመሸፈን አቅም ወደ 86.4 በመቶ ከፍ ማለቱ የሀገር ውስጥ ገቢ አሰባሰብ ሥርዓቱ ይበልጥ ውጤታማ መሆኑን ያሳያል። ከዚህ ጋር ተያይዞም የበጀት ጉድለትን ከ3 በመቶ ወደ 1.6 በመቶ ዝቅ ማድረግ መቻሉ፣ እንዲሁም የውጭ ዕዳ ጫናን ከ30.6 በመቶ ወደ 26.9 በመቶ መውረዱ ለሀገራችን የማክሮ-ኢኮኖሚ ጤናማነት ትልቅ ዋስትና የሚሰጥ ተጨባጭ ለውጥ ነው።
የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ትንሣኤ
ቀደም ሲል በከፍተኛ ዕዳ እና ኪሳራ ውስጥ የነበሩ የመንግሥት የልማት ድርጅቶች፣ ዛሬ አብዛኛዎቹ የሀገራችን የኢኮኖሚ ሞተር መሆን ችለዋል። በ2010 ዓ.ም በአጠቃላይ 8 ቢሊዮን ብር ኪሳራ ያስመዘግቡ የነበሩ ድርጅቶች፣ በሪፎርሙ አማካኝነት ወደ ትርፋማነት ተሸጋግረዋል። በ2018 በጀት ዓመት ዘጠኝ ወራት ውስጥ ብቻ አጠቃላይ ገቢያቸው 2.1 ትሪሊዮን ብር የደረሰ ሲሆን፣ ከታክስ በፊት 351 ቢሊዮን ብር ትርፍ ማስመዝገባቸው፣ እንዲሁም 277.5 ቢሊዮን ብር ታክስ መክፈላቸው ዘርፉ እያስመዘገበ ያለውን አስገራሚ እመርታ ያሳያል።
የኢንዱስትሪው ዘርፍ የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ሽግግር አንቀሳቃሽ ሞተርነት
የሀገራችን የኢኮኖሚ ዕድገት ጥራቱን የጠበቀ እንዲሆን ከማድረግ አኳያ፣ የኢንዱስትሪው ዘርፍ ኢኮኖሚውን የመምራት ተስፋ ሰጪ ጉዞ ጀምሯል። ለጠቅላላ ሀገራዊ ምርት (GDP) ዕድገት የዘርፎችን አስተዋጽኦ ስንመለከት፣ የግብርናው ዘርፍ ድርሻ በ3.6 በመቶ ሲቀንስ፣ የኢንዱስትሪው ዘርፍ ድርሻ ግን በ3 በመቶ አድጓል። ይህ የቁጥር ለውጥ ኢኮኖሚው ቀስ በቀስ ከግብርና ጥገኝነት በመላቀቅ እሴት ወደሚጨምረው የኢንዱስትሪ ዘርፍ በተጨባጭ እየተሸጋገረ መሆኑን ያረጋግጣል። በ"ኢትዮጵያ ታምርት" ንቅናቄ አማካኝነት የፋብሪካዎች የማምረት አቅም በአማካይ በ4 በመቶ ያደገ ሲሆን፣ የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ የተኪ ምርት ድርሻ 58 በመቶ፣ እንዲሁም የኤክስፖርት ገቢው የ45 በመቶ ዕድገት አሳይቷል። የብረት ምርት በ70 በመቶ እና የሲሚንቶ ምርት በ50 በመቶ ማደጋቸውም ዘርፉ በቀጣይ የሀገራችንን ማክሮ-ኢኮኖሚ በዋነኛነት እንደሚዘውር ጠንካራ ማሳያዎች ናቸው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በቅርቡ ከቃና ቴሌቪዥን ጋር ባደረጉት ቆይታ የኢንዱስትሪው ዘርፍ በሦስት እና አራት ዓመታት ቦታውን እንደሚይዝ መናገራቸው የሚታወስ ነው።
የምርት ዘርፎች መነቃቃት እና የቴክኖሎጂ ሽግግር
የግብርናው ዘርፍ በሜካናይዜሽን ታግዞ ምርታማነቱን በከፍተኛ ደረጃ አሳድጓል። የትራክተሮች ቁጥር ከ4 ሺህ 716 ወደ 27 ሺህ 210 በማደጉ፣ የስንዴ ምርት በ33 በመቶ፣ የገብስ ምርት ደግሞ በ41 በመቶ እንዲጨምር አድርጓል። በማዕድን ዘርፍም ለኤክስፖርት የሚቀርበው የወርቅ ምርት በ1 ሺህ 241 በመቶ ማደጉ እና የድንጋይ ከሰል የሀገር ውስጥ ገበያ ድርሻን ከ17 በመቶ ወደ 75 በመቶ ማሳደግ መቻሉ የውጭ ምንዛሬን ከማዳን አኳያ ሚናው የጎላ ነው። በተጓዳኝም የኤሌክትሪክ ምርት በ32 በመቶ ማደጉ ለኢንዱስትሪው ዘርፍ መፋጠን ተጨማሪ ትልቅ አቅም ፈጥሯል።
ዓለም አቀፋዊ ተጽዕኖዎችን መቋቋም እና የወደፊት ተስፋ
ኢትዮጵያ የያዘችው ትክክለኛ የኢኮኖሚ አቅጣጫ በተለያዩ ዓለም አቀፍ ፈተናዎች ውስጥም አዎንታዊ ውጤት እያመጣ ነው። የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት መሳብን በተመለከተ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ብቻ የእቅዱን 100 በመቶ ማሳካት ተችሏል። ይህ ስኬት በመካከለኛው ምሥራቅ ካለው የጂኦፖለቲካዊ ውጥረት እና የዓለም አቀፍ የነዳጅ ዋጋ መዋዠቅ አንፃር ሲታይ፣ ኢትዮጵያ በራሷ አቅም ላይ የተመሰረተ እና አደጋዎችን መቋቋም የሚችል (አይበገሬ) ኢኮኖሚ እየገነባች መሆኑን ያሳያል። በ2018 በጀት ዓመት የ10.2 በመቶ ድርብ አሃዝ የኢኮኖሚ ዕድገት እንደሚመዘገብ መተንበዩ ደግሞ፣ ሀገራችን የጀመረችውን የብልጽግና ጉዞ በማፋጠን የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ያላትን ጠንካራ መሠረት በተግባር የሚያሳይ ነው። ይህ በርካታ ውጫዊ እና ውስጣዊ ተግዳሮቶች መካከል የመጣው ተጨባጭ ለውጥ የኢትዮጵያን ትክክለኛ መስመር የሚያሳይ ከመሆኑም በላይ ሁሉም ሪፎርሙን እኩል ተረድቶ ወደ ተግባር ቢገባ ሊመጣ የሚችለውን አስደናቂ ለውጥ መገንዘብ ማሰብ ይቻላል።
ዓለም አቀፋዊ ምስክርነት
ኢትዮጵያ የያዘችው ትክክለኛ የኢኮኖሚ አቅጣጫ በዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት ዘንድ እውቅናን እያገኘ ነው። የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (IMF) እ.ኤ.አ በ2026 ኢትዮጵያ 9.2 በመቶ ዕድገት በማስመዝገብ ከሰሃራ በታች ያሉ የአፍሪካ ሀገራትን የኢኮኖሚ ዕድገት እንደምትመራ የሰጠው ትንበያ፣ የሀገር በቀል ሪፎርሙ ውጤታማነት ትልቁ ማረጋገጫ ነው።
ለሚ ታደሰ