የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አሕመድ ሽዴ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በመገኘት በ2019 የፌዴራል መንግሥት ረቂቅ በጀት ዙሪያ ለምክር ቤቱ አባላት ማብራሪያ ሰጥተዋል።
ሚኒስትሩ በማብራሪያቸው መንግሥት ባለፉት ሁለት ዓመታት ለበጀት ጉድለት ከብሔራዊ ባንክ ምንም ዓይነት ብድር እንዳልወሰደ ገልጸዋል።
ይህም የዋጋ ንረቱን ለመቆጣጠር በእጅጉ እንደረዳ እና ወደ ነጠላ አኃዝ እንዲወርድ እንዳገዘ ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በፍጥነት እያደጉ ካሉ የዓለም ኢኮኖሚዎች አንዱ ነው። ከ2012 እስከ 2016 ባሉት ዓመታት የ6.8 በመቶ በ2017 ደግሞ የ9.2 በመቶ ዕድገት አሳይቷል። በተያዘው ዓመት ደግሞ የ10.2 በመቶ ዕድገት ይመዘገባል ተብሎ ይጠበቃል።
በነሐሴ 2014 ዓ.ም 34.5 በመቶ ደርሶ የነበረው የዋጋ ንረት በመጋቢት 2018 ዓ.ም ወደ 9.4 በመቶ ማውረድ ተችሏል ብለዋል የገንዘብ ሚኒስትሩ በማብራሪያቸው።
ለኢኮኖሚው ፈጣን ዕድገት ምርት እና ምርታማነት ማረጋገጥ መቻሉ እና የማክሮ ኢኮኖሚው ማሻሻያ ትልቅ ሚና እንደነበራቸውም አብራርተዋል።
ባንኮች ወደ ገበያው የሚለቅቁት የገንዘብ ፍሰት ከኢኮኖሚው ጋር የተጣጣመ መሆኑ እና ውጤታማ የገንዘብ ፖሊሲዎች ትግበራ ለኢኮኖሚ ዕድገቱ አንዱ ግብአት ነበር ብለዋል።
ወደ ገበያ የተደረገው የውጭ ምንዛሬ ሥርዓት ሽግግር የውጭ ምንዛሬ እጥረቱን ከመቅረፉም ባለፈ በሕጋዊ እና በትይይዩ ገበያ መካከል የነበረውን ሰፊ ልዩነት እንዲጠብብ ማድረጉን ጠቁመዋል።
በአጠቃላይ የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርሙ በውጭ ምንዛሬ አስተዳደር ላይ ዘመናዊ እና ውጤታማ ሥራዎች እንዲሠራ አድርጓል ሲሉ የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አሕመድ ሽዴ ገልጸዋል።
በሀብተሚካኤል ክፍሉ